ድኩላ ዝርያው ከኒያላ ወይም ከአጋዘን ይመደባል፡፡ በተለያዩ መልክዓ ምድራዊ ማለትም መካከለኛ ሙቀት ባላቸው፣ በዝናባማና ደን በበዛባቸው ተራራማ አካባቢዎች ይኖራል፡፡ በደረቃማም ሆነ እርጥበታማ ስፍራዎችም መኖር ይችላል፡፡ ከሰሃራ በታች በሚገኙ የአፍሪካ አገሮች የሚገኘው ድኩላ፣ በኢትዮጵያ አንዳንድ ስፍራዎች ለምግብነት ያገለግላል፡፡
ድኩላዎች ፀጉራማ ሲሆኑ፣ ፀጉራቸው እንደሚኖሩበት አካባቢ የአየር ፀባይ የተለያየ ነው፡፡ ቢጫ፣ ቀላ ያለና ቡናማ ቀለም ሲኖራቸው፣ ጥቅጥቅ ባለ ደን ውስጥ የሚኖሩት ጥቁር ፀጉር አላቸው፡፡
ወንዶቹ ብቻ ቀንድ ያላቸው ሲሆን፣ የቀንዳቸው ርዝመትም ከ10 እስከ 20 ኢንች ይደርሳል፡፡ ንቁ ሲሆኑ፣ ይበልጥ የሚነቁት ግን ሌሊት ላይ ነው፡፡ አትክልት/ሳር በሊታ ናቸው፡፡ በሚፈሩበት ወይም የአዳኞቻቸውን ድምፅ በሚሰሙበት ጊዜ መሬት ላይ ለጥ ብለው ማሳለፍን ይመርጣሉ፡፡ የፍርኃት ድምፅም ያሰማሉ፡፡