ዲያቆን ዳንኤል ክብረት የፕሬስ ድርጅት ቦርድ አባል ሆኑ
የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን የተጓደሉ ቦርድ አባላት እንዲሟሉ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) መረራ ጉዲናን (ዶ/ር) የቦርድ አባል፣ እንዲሁም የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትሩን አቶ አህመድ ሺዴ ደግሞ የቦርድ ሰብሳቢ አድርገው ሰየሙ፡፡
የተቃዋሚ ፓርቲ አመራርም ሆነ አባል በእንዲህ ዓይነት የመንግሥት ኃላፊነት በቅርብ ዓመታት ውስጥ ተሰይሞ የማያውቅ በመሆኑ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ መረራ (ዶ/ር) የአገሪቱን ብሔራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ ቦርድ አባል በማድረግ ማቅረባቸው የበርካታ የምክር ቤት አባላትን ቀልብ ገዝቷል፡፡
ከዶ/ር መረራ በተጨማሪ ወ/ሮ ሐሊማ ባድገባና አቶ ፍሰሐ ይታገሱ የተባሉ የፓርላማው አባላትም፣ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ቦርድ አባል ሆነው ተሰይመዋል፡፡
በተመሳሳይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት የቦርድ አባል ሆነው እንዲሰየሙ ለፓርላማው አቅርበዋል፡፡ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታው አቶ ካሳሁን ጎፌ የፕሬስ ድርጅት ቦርድ ሰብሳቢ እንዲሆኑ፣ እንዲሁም አቶ ተካ አባዲ፣ አቶ በቀለ ሙለታ፣ አቶ ዮናስ አስናቀ፣ አቶ ወንድወሰን አንዱዓለም፣ ወ/ሮ ጀሚላ ሽብሩና ወ/ሮ አበበች ሺኮቻ የቦርድ አባላት ሆነው በጠቅላይ ሚኒስትሩ ለፓርላማ ቀርቧል፡፡
ፓርላማውም በጠቅላይ ሚኒስትሩ የቀረበውን ጥያቄ ቅዳሜ ሰኔ 30 ቀን 2010 ዓ.ም. ባካሄደው ልዩ ስብሰባ የኢቢሲን ቦርድ ስያሜ ያጸደቀ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅትን ስያሜ ለማጽደቅ ለሌላ ጊዜ አስተላልፎታል፡፡