Friday, December 8, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

ለክቡር ሚኒስትሩ ደላላ ወዳጃቸው ይደውልላቸዋል

[የክቡር ሚኒስትሩ ሚስት በጣም ተጨናንቀው ተክዘው ቁጭ እንዳሉ ክቡር ሚኒስትሩ ቤት ገቡ]

  • አንተ ምን ሆነሃል ዛሬ?
  • ምን ሆንኩኝ?
  • እንደዚያ ስልክ ስቀጠቅጥልህ የማታነሳው ለምንድነው?
  • ቀኑን ሙሉ ስብሰባ ላይ ነበርኩ፡፡
  • ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስብሰባ ቅዳሜ ቅዳሜ ብቻ ነው ብለዋል አይደል እንዴ?
  • እኔ እኮ አሁንስ በጣም ግራ ግብት እያለኝ ነው፡፡
  • ምኑ ነው ግራ የገባህ?
  • አንቺ ደግሞ ቤቱ ውስጥ ሌላ አለቃ ልትሆኚብኝ ነው?
  • እሱ የእኔ ችግር አይደለም፡፡
  • አለቃ ስለበዛብኝ ሰልችቶኛል እያልኩሽ ነው፡፡
  • እኔ እኮ አለቃ ልሆንብህ ፈልጌ አይደለም፡፡
  • ታዲያ ምን ፈልገሽ ነው?
  • በጣም አንገብጋቢ ጉዳይ ላማክርህ ነው፡፡
  • የምን አንገብጋቢ ጉዳይ?
  • እየተወራ ያለውን ነገር አልሰማህም እንዴ?
  • አገሩ ሁሉ ወሬኛ ብቻ አይደለም እንዴ? ከእኛ ውጪ ማን የሚሠራ አለ ብለሽ ነው? የምን ወሬ ነው?
  • አደገኛ ነገር መጥቷል፡፡
  • እኮ ምኑ ነው አደገኛው ነገር?
  • ቤት ውስጥ በካዝና ያስቀመጥነውን ገንዘብ ምንድነው የምናደርገው?
  • የራሳችን ገንዘብ እኮ ነው፣ እዚሁ ነዋ የሚቀመጠው፡፡
  • የራሳችን ገንዘብ ነው ስትል ትንሽ እንኳን አታፍርም?
  • እና የማን ገንዘብ ነው?
  • የደሃው ሕዝብ ገንዘብ ነዋ፡፡
  • ሴትዮ ዝም ብለሽ አትመፃደቂ፡፡
  • ስማ ያኛው ካዝና የስንት ሺሕ ሰው ኮንዶሚኒየም፣ ያኛው ካዝና ደግሞ የስኳር ፋብሪካዎችን፣ ይኼኛው ደግሞ የማዳበሪያ ፋብሪካውን ገንዘብ የያዙ መሆኑን ረሳኸው?
  • ስሚ አንቺም ከእኔ ጋር መሰለኝ የዘረፍሽው?
  • እኔ አልዘረፍኩም እያልኩህ አይደለም?
  • ታዲያ አንቺን ማን ነው የካዝና ኦዲተር ያደረገሽ?
  • ዋናው ኦዲተር ከመምጣቱ በፊት ራሳችንን ኦዲት ብናደርግ ይሻላል ብዬ ነው፡፡
  • ለምን ዝም ብለሽ ነገር ትቆሰቁሻለሽ?
  • ሰውዬ ጣጣ ሳይመጣብን ይኼን ብር ወደ ዶላር እንቀይረው፡፡
  • እሱንማ ፈጽሞ አላደርገውም፡፡
  • ለምን?
  • ስሚ የዶላር ዋጋ መውደቁን አልሰማሽም እንዴ?
  • እሱማ ሰምቻለሁ፡፡
  • በዚያ ላይ ደግሞ ይኼንን ብር አራጣ እያበደርኩበት መሆኑን ታወቂያለሽ አይደል እንዴ?
  • አራጣ ወንጀል መሆኑን ረሳኸው እንዴ?
  • ሴትዮ እኔ እንዲያውም በቅርቡ ባንክ ለመክፈት እያሰብኩ ነው፡፡
  • የምን ባንክ?
  • ሚኒስትሩ የሚባል ባንክ፡፡
  • ስማ እንደዚህ ዓይነት ዓይን ያወጣ ሌብነት ውስጥ ገብተህ መማማሪያ እንዳያደርጉህ ነው የምፈራው?
  • ምንም ሊያደርጉኝ አይችሉም ስልሽ?
  • የቤት ለቤት አሰሳ ሊጀመር ነው ሲሉ ሰምቻለሁ?
  • የምን አሰሳ ነው?
  • ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሕገወጥ ባንኮች አገሪቱ ውስጥ እንዳሉ ደርሰንበታል ብለዋል፡፡
  • የእኛ በድብቅ ኔትወርክ ስለሚሠራ ማንም አይደርስበትም፡፡
  • ብቻ እኔ ከመዋረዳችን በፊት ዕርምጃ ብንወስድ ጥሩ መሰለኝ፡፡
  • ምን ዓይነት ዕርምጃ?
  • ከቻልን በዶላር መቀየር ካልሆነ ደግሞ ንብረት መግዛት ይሻለናል፡፡
  • ቆይ ገንዘቡን ቆፍረን ብንቀብረውስ?
  • ጠቅላይ ሚኒስትሩ እኮ ወደ ባንክ ካመጣችሁት ሳትጠየቁ በምሕረት ትቀጥላላችሁ ብለዋል፡፡
  • ስሚ ‹ሊበሏት ያሰቧትን ጅግራ ቆቅ ናት ይሏታል› አሉ፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • አሁን እኛ ገንዘባችንን ወደ ባንክ ብናስገባ ማን ይለቀናል?
  • ማን ይነካናል?
  • ስሚ ገንዘባችንን ወደ ባንክ ከተው፣ እኛን ወደ ቂሊንጦ ነው የሚልኩን፡፡
  • ሰውዬ በዚህ አካሄዳችን ግን ባዶአችንን ነው የሚያስቀሩን፡፡
  • እንዴት አድርገው?
  • ሊቀየር ነው እየተባለ ነው፡፡
  • ምን?
  • የብር ኖት!

[ክቡር ሚኒስትሩ ከአንድ የዓረብ አገር ዲፕሎማት ጋር እያወሩ ነው]

  • በጣም ረዥም ጊዜ ሆነን ክቡር ሚኒስትር?
  • ምን እባክህ ሥራ ስለሚበዛብኝ ነው፡፡
  • ለነገሩ ኢትዮጵያ ያለችበት ሩጫ ይገባኛል፡፡
  • የአትሌት አገር ናት ብለው ነው መሰለኝ ይኸው እኛንም እያሯሯጡን ነው፡፡
  • ያው መቼም ሩጫው ለእርስዎ አይከብድዎትም፡፡
  • ኧረ አንዳንዴ ከአቅሜ በላይ እየሆነ ነው፡፡
  • ለነገሩ ዕድሜዎም ስለገፋ ሊያስቸግርዎት እንደሚችል አውቃለሁ፡፡
  • ልባችንን ሊያስተፉን እኮ ነው፡፡
  • ግን ክቡር ሚኒስትር አሁን ያለው አመራር በእውነት የሚያስደስት ነው፡፡
  • እንዴት ማለት?
  • አሁን የአገሪቱ ዋነኛ ችግር የተፈታ ይመስለኛል፡፡
  • ምንድነው የአገሪቱ ዋነኛ ችግር?
  • እኛ ሁሌም የኢሕአዴግ ችግር፣ የችግሩን መንስዔ ውጫዊ ማድረጉ ነው እንላለን፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • ሁሌም ቢሆን እኮ የኢሕአዴግ ዋነኛ ጠላት ኢሕአዴግ ነው ስንላችሁ አትሰሙም ነበር፡፡
  • እየተሳሳትክ እኮ ነው፡፡
  • ኧረ በፍፁም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ምን እያልክ ነው ታዲያ?
  • ችግራችሁ ውስጣችሁ ሆኖ የምትጠቁሙት ግን ወይ ወደ ግብፅ፣ ካልሆነ ደግሞ ኤርትራና ሶማሊያ ላይ ነበር፡፡
  • እነሱማ አሁንም ጠላቶቻችን ናቸው፡፡
  • አይ ክቡር ሚኒስትር አዲሱ አመራር እኮ ይኼን አመለካከት ቀይሮታል፡፡
  • እንዲያውም ዋነኛ ችግራችን የውጭ ኃይሎች እየመጣችሁ በውስጣችን ስለምትፈተፍቱ ነው፡፡
  • አዲሱ አመራር እኮ ከውስጣችሁ የበሰበሰውን ቆርጦ ስለጣለ ነው ሰላም የመጣው፡፡
  • ሰውዬ ብንከባበር አይሻልም? እኔ ነኝ የበሰበስኩት?
  • ኧረ እንደዚያ ለማለት ፈልጌ አይደለም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ኢሕአዴግን እዚህ ያደረስነው እኮ እኛ አንጋፋዎቹ ነን፡፡
  • እሱማ ሀቅ ነው፣ እኔ እንደዚያ አይደለም ያልኩት፡፡
  • ታዲያ ምን እያልክ ነው?
  • የውስጣችሁ ችግር ሲፈታ ይኸው የአካባቢያችሁንም ሰላም በማስጠበቅ ኃያልነታችሁን እያስመሰከራችሁ ናችሁ፡፡
  • የምን ኃያልነት ነው?
  • ይኸው የደቡብ ሱዳን መሪዎችን ከስንት ጊዜ በኋላ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናቸው ያጨባበጧቸው፡፡
  • ምን ይጠበስ ታዲያ?
  • ከዚያም አልፎ ኢትዮጵያ ከኤርትራ ጋር ያላት ጠላትነት አብቅቶ ሁለቱ አገሮች በፍቅር ወድቀዋል፡፡
  • እሱ ላይ እኔ ተቃውሞ አለኝ፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር መሪዎቹ እንዴት ሲፍለቀለቁ እንደነበሩ ሲታይ እኮ ምን ያህል በፍቅር እንደወደቁ ያስታውቃል፡፡
  • እኔ ግን ከኢሕአዴግ ያፈነገጡ አካሄዶችን እያየሁ ነው፡፡
  • የተባለውን ሰምተዋል ግን ክቡር ሚኒስትር?
  • ምን ተባለ?
  • ኤርትራውያን እኮ ባድመን ወስዳችሁ ዓብይን ስጡን እያሉ ነው፡፡
  • ቀልዱን ብትተወው ጥሩ ነው፡፡
  • ለማንኛውም ክቡር ሚኒስትር እኔ አንድ ነገር ሆኛለሁ፡፡
  • ምን?
  • ተደምሬያለሁ!

[ለክቡር ሚኒስትሩ ደላላ ወዳጃቸው ይደውልላቸዋል]

  • እንዴት ነዎት ክቡር ሚኒስትር?
  • ሰላም ነህ?
  • ምነው ድምፅዎ ኮስተርተር አለብኝ?
  • እንዴት አልኮሳተር?
  • አሁንማ ሊስቁበትና ሊፈነድቁበት የሚገባ ጊዜ ነው፡፡
  • ምን ተገኘ ብዬ?
  • ከኤርትራ ጋር ሰላም ወረደ አይደል እንዴ?
  • ታዲያ ሰላም መውረዱ እኔን ለምን ያስፈነድቀኛል?
  • ክቡር ሚኒስትር አየር መንገዱ እኮ ሥራ ሊጀምር ነው፡፡
  • ሰውዬ እኔ እኮ ፓይለት አይደለሁም፡፡
  • ወደቡም በቅርቡ ሥራ መጀመሩ አይቀርም፡፡
  • እኔን መርከበኛ ነው ብሎ የነገረህ ሰው አለ እንዴ?
  • ክቡር ሚኒስትር አንዳንዴ ነገሮችን ሰፋ አድርገው ማየት አለብዎት፡፡
  • ምን እያልክ ነው?
  • ይኼ እኮ ለእኔና ለእርስዎ ትልቅ አጋጣሚ ነው፡፡
  • አልገባኝም?
  • ሁለቱ አገሮች ሰላም ከሆኑ እኮ አዳዲስ ቢዝነሶች አቆጠቆጡ ማለት ነው፡፡
  • የምን አዳዲስ ቢዝነስ?
  • ክቡር ሚኒስትር ኢትዮጵያን በ11 በመቶ ስናሳድጋት ምን ያህል እንደተጠቀምን ያውቃሉ አይደል?
  • እሱማ ልክ ነህ፡፡
  • ኤርትራንም በዚሁ ፍጥነት አሳድገን የድርሻችንን መጠቀም አለብን፡፡
  • እኔ የኤርትራ ማደግ መቼ አስጨነቀኝ አልኩህ?
  • ክቡር ሚኒስትር የኤርትራ ዕድገት ያስጨንቅዎታል ብዬ ሳይሆን የእርስዎን ጥቅም አስቤ ነው፡፡
  • የእኔ ጥቅም ምንድነው?
  • እርስዎ እንደ ምንም ብለው የኢትዮጵያ ገንዘብ ኤርትራ ውስጥ እንዲሠራ ያስደርጉ፡፡
  • ለምን ተብሎ?
  • እዚህ በጥሬው የያዝነውን ገንዘብ እዚያ ይዘን ሄደን መሥራት እንችልበታለና፡፡
  • እንዴት? እንዴት?
  • አዩ ቤት ያለው ገንዘባችን ሕገወጥ ነው ሊባል ስለሚችል፣ ኤርትራ ወስደነው ኢንቨስት ልናደርገው እንችላለን፡፡
  • ለሚስቴ ጭንቀት መፍትሔ  ተገለኘት ነው የምትለኝ?
  • ክቡር ሚኒትር ቆሻሻው ብራችን እዚያ ታጥቦ ይነፃል፡፡
  • የት?
  • ቀይ ባህር!

[ለክቡር ሚኒስትሩ አንድ ዳያስፖራ ይደውልላቸዋል]

  • ክቡር ሚኒስትር እንዴት ነዎት?
  • እንዴት ነህ?
  • ያው እኛም ይመጣሉ ብለን ዝግጅቱን አጧጡፈነዋል፡፡
  • ማን ነው የሚመጣው?
  • ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሊመጡ አይደል እንዴ?
  • አዎ ይመጣሉ፣ እውነትህን ነው፡፡
  • እርስዎ አይመጡም እንዴ?
  • ያው የዶላር እጥረት ስላለ እንደ ድሮው ተግተልትለን መሄድ ቀርቷል፡፡
  • ለነገሩ እርስዎ እዚህ ከመጡ ከፍተኛ ተቃውሞ ነው የሚገጥምዎት፡፡
  • ዋናው የአገሬ ሕዝብ ከወደደኝ ችግር የለውም፡፡
  • ለማንኛውም እዚህ የሕዝቡ ደስታ ወደር የለውም፡፡
  • ምን ተገኝቶ?
  • ልትበተን የነበረችው ኢትዮጵያ ይኸው ሰላሟ ተጠብቆ በሚገርም ፍጥነት እየሄደች ነዋ፡፡
  • እ. . .
  • ክቡር ሚኒስትር የውስጥ ችግራችን ተፈትቶ በአካባቢው ላይ ተፅዕኖ ፈጣሪ መሆናችን እየታየ ነው፡፡
  • እሱን እንኳን ተወው፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ከግብፅ ቢሉ ከኤርትራ ጋር በምናደርገው ነገር በዓለም አቀፍ ደረጃ እየተደነቅን ነው፡፡
  • ተደምረሃል ልበል?
  • ከተደመርኩማ ቆየሁ፡፡
  • አሁን ገባኝ፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር እዚህ አገር የፕሬዚዳንቱ አንድ መቶ ቀናት የሚባል ነገር አለ፡፡ የእኛም ጠቅላይ ሚኒስትር በዚህ ሳምንት መቶ ቀናት ይሞሉዋቸዋል፡፡
  • ታዲያ ምን ይጠበስ?
  • መቼም ኢሕአዴግ ነፃ ምርጫ ሳያደርግ መቶ በመቶ አሸንፌያለሁ ማለቱን ያምናሉ?
  • ሰውዬ እኛ በትክክለኛ ምርጫ ነው ያሸነፍነው፡፡
  • እሱን ይተውትና ሕዝቡ አዲሱን ጠቅላይ ሚኒስትር በመቶ ቀናት ውስጥ ፈትኖ ውጤት ሰጥቷል፡፡
  • ስንት ተሰጣቸው?
  • መቶ በመቶ!

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

ታዋቂው የኤሌክትሮኒክስ ብራንድ አይቴል የስትራቴጂ ለውጥ አካል የሆነውን አዲስ አርማ እና መለዮ ይፋ አደረገ።

በአለማችን ታዋቂ ከሆኑት የኤሌክትሮኒክስ ብራንዶች መካከል አንዱ የሆነው እና...

የጠቅላላ ጉባኤ ስብሰባ ጥሪ ለሸገር አነስተኛ የፋይናንስ ተቋም አ.ማ ባለአክሲዮኖች በሙሉ

ለሸገር አነስተኛ የፋይናንስ ተቋም አ.ማ ባለአክሲዮኖች በሙሉ የሸገር አነስተኛ የፋይናንስ...

[የክቡር ሚኒስትሩ ጸሐፊ፣ የሌላ ሚኒስትር ጸሐፊ ከሆነችው የቅርብ ወዳጇ ጋር በስልክ እየተጨዋወቱ ነው]

አንቺ ግን ምን ሆነሽ ነው? ጠፋሁ አይደል? ጠፋሁ ብቻ?! ምን ላድርግ ብለሽ...

በሱዳን ላይ ያጠላው የመከፋፈል ዕጣና ቀጣናዊ ተፅዕኖው

የሱዳን ጦርነት ስምንተኛ ወሩን እያገባደደ ይገኛል፡፡ ጄኔራል አብዱልፈታህ አልቡርሃን...

ኦሮሚያ ኢንሹራንስ በግሉ ኢንሹራንስ ዘርፍ ሁለተኛውን የገበያ ድርሻ ለመያዝ ያስቻለውን ውጤት ማስመዝገቡን ገለጸ

ኦሮሚያ ኢንሹራንስ ኩባንያ የባንኮች የጥሬ ገንዘብ እጥረት፣ የመለዋወጫ ዕቃዎች...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[የክቡር ሚኒስትሩ ጸሐፊ፣ የሌላ ሚኒስትር ጸሐፊ ከሆነችው የቅርብ ወዳጇ ጋር በስልክ እየተጨዋወቱ ነው]

አንቺ ግን ምን ሆነሽ ነው? ጠፋሁ አይደል? ጠፋሁ ብቻ?! ምን ላድርግ ብለሽ ነው? እንዴት? አለቃዬ ዕረፍት የለው፣ እኔንም አላፈናፍን ብሎኛል። ታድለሽ። ታድለሽ? ሥራ ገደለኝ ዕረፍት አጣሁ እኮ ነው ያልኩሽ? ገብቶኛል። ምነው እኔንም...

[ክቡር ሚኒስትሩ የሩብ ዓመት የሥራ አፈጻጸማቸውን ለተከበረው ምክር ቤት ካቀረቡ በኋላ ከምክር ቤቱ አባላት የሚነሱ ጥያቄዎችን እየተቀበሉ ማብራሪያ በመስጠት ላይ ናቸው]

ክቡር ሚኒስትር መንግሥት ለሕዝብ ይፋ ያደረገው ነገር ከምን እንደደረሰ ቢያብራሩልን? ምንድነው ይፋ ያደረገው? ጥያቄውን ትንሽ ቢያብራሩት? ከአራት ዓመት በፊት በኦጋዴን አካባቢ ነዳጅ መገኘቱን ለሕዝብ በቴሌቪዥን አብስሮ...

[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ የካቢኔና የማክሮ ኢኮኖሚ ኮሚቴ አባል የሆኑ ከፍተኛ አመራር የሚያቀርቡትን ቅሬታ እያደመጡ ነው] 

ክቡር ሚኒስትር እየሆነ ያለው ነገር በእጅጉ ስላሳሰበኝ ነው በአካል አግኝቼ ላነጋግርዎት የፈለግኩት። ጥሩ አደረግህ፣ ምን አሳሳቢ ነገር ገጥሞህ ነው? ክቡር ሚኒስትር ተወያይተንና ተግባብተን ያስቀመጥናቸው አቅጣጫዎች፣ በተለይም...