ኢትዮጵያ የአፍሪካ የንግድ ኢንሹራንስ (መድን) ኤጀንሲ አባል ለመሆን የሚያስችላትን ስምምነት በፓርላማው ሊፀድቅ ነው፡፡
የስምምነቱ ማፅደቂያ አዋጅ ማክሰኞ መጋቢት 13 ቀን 2008 ዓ.ም. ለፓርላማው፣ ቀርቦ ለዝርዝር ዕይታ ወደ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ተመርቷል፡፡
ኢትዮጵያ የኤጀንሲው አባል ለመሆን ጠይቃ በኤጀንሲው ቦርድ ሲፈቀድላት፣ ቀጥሎም የተሳትፎ ስምምነት ማለትም የአባልነት ጥያቄ ባቀረበው አገርና በኤጀንሲው መካከል ስለሚኖር መብትና ግዴታዎች፣ እንዲሁም የዋስትና ሽፋኑን አፈጻጸም ዝርዝር የተመለከተ ስምምነት መፈረም ይኖርባታል፡፡
ነገር ግን ይህንን ስምምነት ለመፈራረም መጀመሪያ የኤጀንሲው አባል ለመሆን ጥያቄውን ያቀረበው አገር በሕግ አውጪው በኩል ስምምነቱን ማፅደቅ የሚኖርበት በመሆኑ፣ ለፓርላማው ሊቀርብ መቻሉን የማፅደቂያ ረቂቅ አዋጁ ማብራሪያ ያስረዳል፡፡
ኢትዮጵያ የዚህ ኤጀንሲ አባል ብትሆን የፖለቲካና የንግድ ብድር ዋስትና ማግኘት የሚያስችላት ከመሆኑም በላይ፣ እነዚህ የመድን አገልግሎቶች በኢትዮጵያ የማይሰጡ በመሆናቸው ጥቅማቸው የጐላ መሆኑን ማብራሪያው ይገልጻል፡፡
ኢትዮጵያ የኤጀንሲው አባል ለመሆን የ75 ሚሊዮን ዶላር አክሲዮን ድርሻ ሊኖራት የሚገባ ሲሆን፣ ይህንንም ገንዘብ ከአፍሪካ ልማት ባንክ በብድር ማግኘቷ ተገልጿል፡፡ ይህ የብድር ስምምነት ማፅደቂያ ረቂቅ አዋጅም ለፓርላማው ተያይዞ ቀርቧል፡፡ ፓርላማው ሁለቱን አዋጆች ለዝርዝር ዕይታ ለበጀትና ለፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ መርቶታል፡፡