የታሪክ ድርሳናት እንደሚያስረዱት በኢትዮጵያ ታሪክ ፈረስ ልዩ ስፍራ አለው፡፡ የቀድሞዎቹ ነገሥታትና መኳንንት የክብራቸውም የጀግንነታቸውም መገለጫ ሆኖ ቆይቷል፡፡ በዚህ ብቻም ሳይወሰን ስማቸውን ጭምር በፈረሶቻቸው ሲሰይሙ ኖረዋል፡፡
በምንገኝበት ዘመን ደግሞ በተለይ በአውሮፓና ሌሎችም ዓለማት የፈረስ ስፖርት ከባህላዊው መንገድ ተላቆና በዘመናዊ ስፖርትነቱ ዓለም ላይ ከሚወደዱና ከሚዘወተሩ ስፖርቶች ተርታ ይገኛል፡፡ ለዚህ ማሳያ የሚሆነው ደግሞ በአሜሪካ በስፋት እየተዘወተረ የሚገኘውና በመደበኛ የውድድር መርሐ ግብር የሚከናወነው ‹‹የኬንታኪ ደርቢ›› አንዱና ዋናው ሲሆን፣ በተመሳሳይም በእንግሊዝና በዱባይ በሌሎችም አገሮችም የፈረስ ስፖርት ሲዘወተር ይስተዋላል፡፡
የፈረስ ስፖርት ምንም እንኳ በኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት በዓለም እንደሚዘወተረው ዘመናዊ አሠራርን የተከተለ ባይሆንም ወደ ነበረበት ዝናውና ክብሩ ለመመለስ ጥረት እየተደረገ መሆኑ በቅርቡ የኢትዮጵያ ፈረስ ስፖርት አሶሴሽን ፕሬዚዳንት በመሆን የተመረጡት አቶ ጌታቸው ሥዩም ይናገራሉ፡፡ እንደ አቶ ጌታቸው ከሆነ፣ የኢትዮጵያ ፈረስ ስፖርት ከሁለት አሠርታት በፊት በነበረው ስምና ዝናው በብሔራዊ ፌዴሬሽን ደረጃ የተቋቋመ ቢሆንም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን ስፖርቱ በአገር አቀፍ ደረጃ እየተቀዛቀዘ በመምጣቱ ምክንያት በአሶሴሽን ደረጃ ሊጠራ መቻሉንም ያስረዳሉ፡፡
ባለፈው እሑድ መጋቢት 18 ቀን 2008 ዓ.ም. በፈረስ ስፖርት ቀደምቱ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን አዘጋጅነት ሰባት ክለቦች ማለትም የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የፈረስ ስፖርት ክለብ፣ ሜጀር ጄኔራል ኃየሎም አርአያ የፈረስ ስፖርት ክለብ፣ ባልደራስ የፈረስ ስፖርት ክለብ፣ በአዲስ አበባ ሶሳይቲ የፈረስ ስፖርት ክለብ፣ በፍሬተር የፈረስ ስፖርት ክለብ፣ በቤካ ፈርዳ ራንች የፈረስ ስፖርት ክለብና በጣሊያን ኤምባሲ ፈረስ ስፖርት ክለብ መካከል በተለያየ የዕድሜ ደረጃ (ካታጎሪ) የተለያየ ውድድር ተከናውኗል፡፡ በዚሁ መሠረት ዕድሜያቸው ከዘጠኝ እስከ 12 በሚገኝ ታዳጊ ወጣቶች መካከል በተደረገው ፉክክር ከጣሊያን ኤምባሲ ሂዛሪ ክሩቤት በሲሊበር ፈረስ አሸናፊ ስትሆን፣ ሁለተኛና ሦስተኛ የወጡት ደግሞ አሁንም በሲልቨር ፈረስ የተወዳደረችው አሊናና በጨፌ ፈረስ የተወዳደረው ሳሌም መሐመድ ከጣሊያን ኢምባሲ ናቸው፡፡
በወጣቶች መካከል ባደረገው ሌላው ውድድር ደግሞ ጃኮቭ ተሰማ በአፍሪካ ከቤካ ፈረዳ ራንች፣ አዲሱ ደጀኔ በአባ መላ ከሜጀር ጄኔራል ኃየሎም አርአያና ሐምጃድ ሳኒ በአዳዋ ከጣሊያን ኤምባሲ ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ያጠናቀቁ ናቸው፡፡
በአዋቂዎች መካከል በቀለ ቱሉ በክራውን ከአዲስ አበባ ሶሳይቲ፣ ደረጃ ኃይሌ በኒል ሐልቲ ከባልደራስ፣ ሳኒ አህመድ በሚራጀ ከጣሊያን ኤምባሲ ባስመዘገቡት ነጥብ ተከታትለው በመግባት አሸናፊ ሆነዋል፡፡ በፈረስ ስፖርት ውድድር ‹‹ሐንተንግ›› ተብሎ በሚጠራው ወይም በ‹‹ሲ›› በ‹‹ቢ›› እና በ‹‹ኤ›› በሦስት ደረጃ ተከፋፍለው በሚከናወኑ ተጨማሪ ውድድሮች ተከናውነዋል፡፡ በዚሁ መሠረት በ‹‹ሲ›› ደረጃ ከቀረቡት ተወዳዳሪዎች አሥር አለቃ ምሕረቱ ዓለሙ በድሬዳዋ ከሜጀር ጄነራል ኃየሎም አርአያ፣ ዳንኤል አብርሃም በፕሪንስ ከቤካ ፈርዳ ራንችና ፓውሎ ያኩና በተድላ ከጣሊያን ኤምባሲ ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ደረጃ በመያዝ አጠናቀዋል፡፡
በ‹ሲ›› ደረጃ ከቀረቡት ተወዳዳሪዎች ደግሞ አህመድ ሳኒ በአፍሪካ ከጣሊያን ኤምባሲ አንደኛ ሲሆን፣ ምክትል ሳጅን ደጉ እሸቱ በጭራ ከባድ ከአዲስ አበባ ፖሊስ ሁለተኛ በመሆን አጠናቋል፡፡ በውድድሩ ሕግ መሠረት ሦስተኛ ለመሆን የተወዳዳሪዎች ብቃት ሊመጥን ባለመቻሉ አልተመዘገበም፡፡
በ‹‹ኤ›› ደረጃ ከቀረቡት ተወዳዳሪዎች ደግሞ ዓብይ በሪሁን በራስ ከቤካ ፈርዳ ራንች፣ አሸናፊ በቀለ በሲሊቨር ከአዲስ አበባ ሶሳይቲና በድጋሚ ዓብይ በሪሁን በኦሪዮን ከቤካ ፈርዳ ራንች ከአንደኛ አስከ ሦስተኛ ያለውን ደረጃ በመያዝ አጠናቀዋል፡፡
የአሶሴሽኑ ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው ሥዩም፣ ውድድሩ ተዳክሞ የቆየውን የፈረስ ስፖርት ለማነቃቃት ይቻል ዘንድ ታቅዶ የተደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በቀጣይም ይህንኑ አጠናክሮ ለመቀጠል ማቀዳቸውንና በተለይም የፈረስ ስፖርትን በመላ አገሪቱ ለማስፋፋትና ያለውን የማዘውተሪያ እጦት ለመቅረፍ ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጋር እየተነጋገሩ ስለመሆኑም አክለዋል፡፡ በዕለቱ በተከናወነው ውድድር በክብር እንግድነት የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ተስፋዬ ዴንደና ተገኝተዋል፡፡