በፌዴራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር በቂሊንጦ እስረኛ ማቆያ የሚገኙ እስረኞች፣ የሠሩት ወንጀል ስለሌለ ከእስር መፈታት እንዳለባቸው በመግለጽ ከሐምሌ 5 ቀን 2010 ዓ.ም. ምሽት ጀምሮ ተቃውሞ አሰሙ፡፡
እስረኞቹ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ይፈቱ ማለታቸውን ጠቁመው፣ የማረሚያ ቤቱ አስተዳደር እንዲፈታቸው በቡድን ሆነው ጥያቄ ማቅረባቸውን የሪፖርተር ምንጮች ገልጸዋል፡፡ ማረሚያ ቤቱ በበኩሉ የተሰጠው ሥልጣን እስረኛን ማስተዳደር እንጂ መፍታት እንዳልሆነ ምላሽ መስጠቱም ታውቋል፡፡
እስረኞችን መፍታትና ክስ የማቋረጥ መብት የፍርድ ቤትና የጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ መሆኑን በመጠቆም፣ አስተዳደሩ ጥያቄያቸውን እንደሚያቀርብም ቢነግራቸውም እስረኞቹ ግን ጥያቄያቸውን ከፍ ባለ ድምፅ ሲያቀርቡ ተሰምቷል፡፡
ዓርብ ሐምሌ 6 ቀን 2010 ዓ.ም. ማለዳ ታሳሪ ቤተሰቦቻቸውን ለመጠየቅና ምግብ ለማቀበል በቂሊንጦ የተገኙ የታሳሪ ቤተሰቦች፣ እንዳይገቡ በመከልከላቸው በከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ መቆየታቸውን ተናግረዋል፡፡ ከውስጥ ጩኸት ይሰሙ ስለነበር፣ ‹‹ቤተሰቦቻችን ምን ሆነው ይሆን?›› በማለት እርስ በርሳቸው ከመጠያየቅ ያለፈ ምላሽ የሚሰጣቸው ያጡት ቤተሰቦች፣ ቁጥራቸው እየጨመረ ሲመጣ በቡድን ሆነው ወደ ማረሚያ ቤቱ መጠጋታቸውን አስረድተዋል፡፡ ምን እየተከናወነ እንደሆነ በከፍተኛ ጩኸት ሲጠይቁ፣ የማረሚያ ቤቱ ጠባቂዎች ምንም ሳይነኳቸው ‹‹ማስገባት አንችልም›› በማለት ብቻ ሲከላከሉ መቆየታቸውን ጠቁመው፣ ሕዝቡ እየበዛና ጩኸት እያየለ ሲመጣ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን አባላት እንዲበተኑ ማድረጋቸውን አስረድተዋል፡፡
ታሳሪ ቤተሰቦቻቸው ምግብ እንደሌላቸውና ምግብም አይገባም በመባሉ መጨነቃቸውን የተናገሩት የታሳሪዎች ቤተሰቦች፣ የሚመለከተው አካል በፍጥነት ምላሽ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፡፡ ይዘውት የሄዱትን ምግብ ወደ ጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በመውሰድ አቤቱታ ለማቅረብ መሄዳቸውንም ገልጸዋል፡፡
የታሳሪዎቹ ጥያቄ ‹‹እንፈታ›› ብቻ መሆን አለመሆኑን ለማጣራት የፌዴራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ኃላፊዎችን ለማግኘት ጥረት ቢደረግም አልተሳካም፡፡