የኢትዮጵያ መርከቦች የኤርትራን የኤክስፖርት ምርት በቅርቡ ወደ ቻይና ማጓጓዝ ይጀምራሉ
ኢትዮጵያና ኤርትራ በቅርቡ በመሀላቸው ሰላም ካሰፈኑ በኋላ የምፅዋ ወደብ ለኢትዮጵያ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል በመሆኑ፣ አገልግሎቱን ለመጀመር በሁለቱም መንግሥታት በኩል ዝግጅቶች እየተደረጉ ነው፡፡
በኢትዮጵያ በኩል የኢትዮጵያ ማሪታይም ባለሥልጣን የሚያስተባብረው ዝግጅት እየተከናወነ መሆኑን ሪፖርተር ያገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
የኤርትራ መንግሥት ሁሉንም የትራንስፖርት አገልግሎቶች ማለትም የአየር፣ የባህርና የየብስ መስመሮችን ለኢትዮጵያ ክፍት ያደረገ መሆኑን፣ በዚህ መሠረት የአስመራ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ፣ የምፅዋና የአሰብ ወደቦች ለኢትዮጵያ አገልግሎት እንዲሰጡ ፈቅዷል፡፡
በኢትዮጵያ በኩል የተቋቋመው ግብረ ኃይል የኤርትራን የወደብ አማራጮች ለመጠቀም በሚቻልበት ሁኔታና ቅድመ ዝግጅቶት ላይ እየመከረ መሆኑን፣ በቅርቡም ውሳኔ በማሳለፍ አገልግሎቱን መጠቀም እንደሚጀምር ምንጮች ገልጸዋል፡፡ ሁለቱ አገሮች ሰላም በማስፈናቸው ምክንያት ከ20 ዓመታት በኋላ የተገኘውን ተጨማሪ የወደብ አማራጭ ለመጠቀም፣ የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ዝግጅቱን ከማጠናቀቅ አልፎ ከምፅዋ ወደብ ተነስቶ ጉዞ ለመጀመር የሚያስችል ጭነት ማግኘቱን ጭምር፣ የድርጅቱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሮባ መገርሳ ገልጸዋል፡፡
‹‹በእኛ በኩል ባደረግነው ግምገማ የምፅዋ ወደብ አሁን ባለበት ሁኔታ የእኛን መርከቦች ለማስተናገድ በቂ ነው፤›› ብለዋል፡፡
‹‹የሁለቱን አገሮች ዳግም ወደ ወዳጅነት መመለስ የሚስችለንን ጭነት ተወዳድረን አግኝተናል፤›› ያሉት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ ‹‹የኤርትራን የኤክስፖርት ምርት ከምፅዋ ወደብ ወደ ቻይና ለማጓጓዝ ውሉ በመጠናቀቅ ላይ ነው፡፡ የምንጠብቀው የመንግሥት ውሳኔ ነው፤›› ብለዋል፡፡
የምፅዋ ወደብ አስተዳዳሪ አቶ ላይኔ አስፋሃለይ ወደቡ አስፈላጊው ዕድሳት ተደርጎለት አገልግሎት ለመስጠት ዝግጁ መሆኑን፣ ሪፖርተርን ጨምሮ ለሌሎች ሚዲያዎችና ወደቡን መጎብኘት ለቻሉ የኢትዮጵያ የንግድ ማኅበረሰብ አባላት ተናግረዋል፡፡
ወደቡ ለኢትዮጵያ አገልግሎት መስጠት ሲጀምር ለኢትዮጵያ የወደብ አማራጭ ከመስጠት ባለፈ፣ የኢትዮጵያን ንግድ አጋሮች ለማዳረስ የሚደረገውን የባህር ላይ ጉዞ የሚያሳጥር፣ እንዲሁም ለሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል የወጪ ንግድ እንቅስቃሴ የበለጠ አዋጭ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡
የምፅዋ ወደብ ከአሰብ ቀጥሎ ሁለተኛው የኤርትራ የባህር ወደብ ሲሆን፣ በ19ኛው ክፍል ዘመን በቅኝ ገዥዎች እንደተገነባ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡