– ከፍተኛ የአካል ጉዳት የደረሰባቸው አምስት ሰዎች ተርፈዋል
በኦሮሚያ ክልል በሻሸመኔ ከተማ በአሌሉ ክፍለ ከተማ ቀበሌ አሥር ውስጥ፣ መቼ እንደተቆፈረና እንደተደፈነ በማይታወቅ ጥልቀት ባለው የመፀዳጃ ቤት ጉድጓድ ላይ ለአምልኮ ማካሄጃ በተሠራ አዳራሽ ውስጥ፣ 18 ሰዎች በፀሎት ላይ እያሉ መፀዳጃ ቤቱ በመደርመሱ አሥር ሰዎች መሞታቸው ተገለጸ፡፡
ሰኞ ሚያዝያ 3 ቀን 2008 ዓ.ም. ከቀኑ 10፡30 ሰዓት አካባቢ በደረሰው አደጋ 18 ሰዎች ጉድጉዱ ውስጥ የሰመጡ ቢሆንም፣ ለሰባት ሰዓታት በተደረገ ከፍተኛ ጥረት የስምንቱን ሰዎች ሕይወት ለማትረፍ መቻሉን፣ የሻሸመኔ ከተማ ፖሊስ መምርያ ኃላፊ ምክትል ኢንስፔክተር ታምራት አበበ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
መፀዳጃ ቤቱ የተቆፈረው መቼ እንደሆነ እንደማይታወቅና ይዞታው ግን የመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ መሆኑን የገለጹት ኃላፊው፣ ያስቆፈሩት ግለሰብ መሞታቸውንና ‹‹ሕያው የእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን›› የሚባለው የአምልኮ ማካሄጃ አዳራሽ ከተገነባ አንድ ዓመት እንደሆነው ገልጸዋል፡፡
ወደታች ሰባት ሜትር ጥልቀት ያለው ጉድጓድ በመሆኑ የሰመጡትን ሰዎች ለማውጣት በጣም አስቸጋሪ እንደነበር፣ ነገር ግን የአካባቢው ነዋሪዎችና ፌዴራል ፖሊስ ወደ ሥፍራው በመሄድ፣ በመቆፈሪያ ማሽን እየተቆፈረ የስምንት ሰዎችን ሕይወት ለማትረፍ መቻሉን ምክትል ኢንስፔክተር ታምራት ገልጸዋል፡፡ ከተረፉት ሰዎች አምስቱ ከፍተኛ የአካል ጉዳት እንደደረሰባቸውም አስረድተዋል፡፡
ሕይወታቸው ካለፈው ፀሎተኞች መሀል አንዲት እናት ከአንድ ዓመት ሕፃን ልጇ ጋር፣ የሦስት ዓመት ታዳጊና የአንድ ቤተሰብ አባላትም እንደሚገኙበት ኃላፊው ተናግረዋል፡፡ ለአደጋው መንስዔ ጉድጓዱ ከተቆፈረ በኋላ በድንጋይና በአፈር በደንብ ተጠቅጥቆ ባለመሞላቱ ሊሆን ይችላል የሚል ግምት ቢወሰድም፣ እስከሚጣራ ድረስ ግን በወቅቱ ስብከቱን ያካሂዱ የነበሩ ግለሰብ በቁጥጥር ሥር ውለው እየተጣራ መሆኑን፣ ምክትል ኢንስፔክተር ታምራት አክለው አስረድተዋል፡፡