በታምሩ ጽጌና በዳዊት እንደሻው
ሐሙስ ሐምሌ 19 ቀን 2010 ዓ.ም. በመስቀል አደባባይ ሞተው የተገኙት ኢንጂነር ስመኘው በቀለ፣ በግራ ጆሮ ግንዳቸው ላይ በጥይት መመታታቸውን የፌዴራል ፖሊስ አስታወቀ፡፡
የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጄኔራል ዘይኑ ጀማል ዛሬ ከቀትር በኋላ በሰጡት መግለጫ፣ ሟቹ ኢንጂነር ስመኘው በሽጉጥ ከጆሯቸው ከበስተጀርባ በግራ በኩል መመታታቸውንና ፖሊስ ምርመራ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ኢንጂነር ስመኘው ጠዋት 1፡30 ሰዓት ቢሮ ገብተው መውጣታቸውን፣ መኪናቸውም በሞቱበት ሥፍራ ከጠዋቱ 2፡30 ሰዓት አካባቢ መገኘቱን ተናግረዋል፡፡
ዛሬ ማለዳ የሰሌዳ ቁጥሩ ኮድ 3 አ.አ. A29722 የሆነ ላንድክሩዘር መኪና ውስጥ መስቀል አደባባይ ሞተው የተገኙ ሲሆን፣ መኪናውም አገር አቋራጭ አውቶቡሶች መንገደኞችን የሚጭኑበትና የሚያወርዱበት ሥፍራ ላይ ቆሞ ነበር፡፡
መኪናው የቆመበት ቦታም ከሌሊቱ አሥር ሰዓት ጀምሮ በመንገደኞች፣ በመኪኖችና በቦታው የስፖርታዊ እንቅስቃሴ በሚያደርጉ ሰዎች እንደሚጨናነቅ ይታወቃል፡፡ ኢንጂነር ስመኘው የሾፌሩ መቀመጫ ላይ ኮፍያና የአንገት ስካርፍ አድርገው የነበረ ሲሆን፣ የአንገታቸው ግራ ጎን በጥይት መመታቱን በሥፍራው የተገኘው የሪፖርተር የጋዜጠኞች ቡድን ለማየት ችሏል፡፡
በመኪናው ውስጥ ሽጉጥ የተገኘ ሲሆን፣ የመኪናው በሮች ቢቆለፉም ሞተሩ አልጠፋም ነበር፡፡ ወደ ሥፍራው የተንቀሳቀሰው የፖሊስ ኃይል የተለያዩ የመረጃዎችን ከሰበሰበ በኋላ፣ ረፋድ 4፡57 ሰዓት አካባቢ መኪናው የቆመበትን ቦታ ከልሎታል፡፡
በሥፍራው ብዛት ካላቸው በአካባቢው ከተገኙ ሰዎች በተጨማሪ፣ የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጄኔራል ዘይኑ ጀማል፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አዜብ አስናቀ፣ የውኃ፣ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስትር ስለሺ በቀለ (ዶ/ር) ተገኝተዋል፡፡