Tuesday, November 28, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊአዲስ ስኬት ፓርክ

አዲስ ስኬት ፓርክ

ቀን:

ከጥቂት ዓመታት በፊት ኢትዮጵያ ውስጥ ስኬት የሚያደርግ ሰው ማግኘት ከባድ ነበር፡፡ በምዕራባውያኑ የተጀመረው ስኬቲንግ (ከእንጨት በተሠራና ጎማ ባለው ቦርድ መንቀሳቀስ) በአጭር ጊዜ በመላው ዓለም የተስፋፋ ሲሆን፣ ዛሬ ዛሬ ኢትዮጵያ ውስጥም እየተለመደ መጥቷል፡፡ ስኬቲንግ አሁንም በአገሪቱ በብዙዎች ባይዘወተርም በዋነኛነት በአዲስ አበባና በአንዳንድ የክልል ከተሞች እየተስፋፋ ነው፡፡

ከዓመታት በፊት ስኬቲንግን አዲስ አበባ ውስጥ የጀመሩት ወጣቶች ተሰባስበው ኢትዮጵያ ስኬት የተባለ ድርጅት ያቋቋሙት የስኬቲንግ መስፋፋትን ታሳቢ በማድረግ ነበር፡፡ ድርጅቱ ታዳጊዎችን ስኬቲንግ በማሠልጠንና ስኬት ቦርድ እንዲያገኙ በማድረግ ለዓመታት ሠርቷል፡፡ ቅዳሜ ሚያዝያ 8 ቀን 2008 ዓ.ም. ደግሞ ለአገሪቱ የመጀመርያ የሆነውን የስኬቲንግ ፓርክ አስመርቀዋል፡፡ ላፍቶ ሞል ጀርባ የተገነባው ፓርኩ አዲስ ስኬት ፓርክ የሚባል ሲሆን፣ ድርጅቱ ሜክ ላይፍ ስኬት ላይፍ ከተባለ የውጭ ተራድኦ ድርጅት ጋር በመተባበር አሠርቶታል፡፡

ፓርኩ የተሠራው ከተለያዩ አገሮች በተውጣጡ በጎ ፈቃደኛ የስኬት ፓርክ ገንቢዎች እንደሆነ የኢትዮጵያ ስኬት የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያና የስኬተሮቹ ሐኪም ዶ/ር ሚካኤል ባህሩ ይናገራል፡፡ ወደ 60 የሚደርሱት በጎ ፈቃደኛ ባለሙያዎች ግንባታውን ሲያካሂዱ የድርጅቱ አባላት ደግሞ በድረ ገጽ እንዲሁም የተለያዩ መዝናኛ ዝግጅቶች በማሰናዳት ገንዝብ ያሰባስቡ ነበር፡፡ ዶ/ር ሚካኤል እንደሚለው፣ የስኬተሮች ቁጥር እየጨመረ ስለሄደና ለስኬቲንግ ምቹ ቦታዎች ለማግኘት ስለሚያስቸግር ስኬት ፓርክ አስፈላጊ ሆኖ አግኝተውታል፡፡

ከዓመታት በፊት ጥቂቶች ስኬቲንግን ሲጀምሩ በየመንገዱ በተናጠል ስኬት በማድረግ ነበር፡፡ ኢትዮጵያ ስኬት እንቅስቃሴ ሲጀምር ስኬተሮቹን ከማሰባሰቡ ጎን ለጎን ለታዳጊዎች ሥልጠና መስጠት ጀመሩ፡፡ ስለ ስኬቲንግ ያለውን ግንዛቤ ለማስፋትም ከቦታ ቦታ እየተዘዋወሩ በቡድን ስኬት ያደርጋሉ፡፡ የድርጅቱ ዳይሬክተርና ቪዲዮግራፈር አሜሪካዊው ሾን ስትሮንዞ ከአራት ዓመት በፊት ወደ ኢትዮጵያ ከመጣበት ጊዜ ጀምሮ ታዳጊዎች ስኬት ቦርድ በዕርዳታ እንዲያገኙ የማድረግ እንቅስቃሴ ጀምረዋል፡፡ ታዳጊዎቹ ቦርዱ ቢኖራቸውም በነፃነት ስኬት የሚያደርጉባቸው ምቹ ቦታዎች ግን ውስን ናቸው፡፡ ፓርኩ ለዚህ ችግር መፍትሔ እንደሚሆንም የድርጅቱ አባላት ተስፋ ያደርጋሉ፡፡

ድርጅቱ በዋነኛነት ሥልጠና የሚሰጠው ከሦስት ዓመት ጀምሮ ላሉ ታዳጊዎችና ወጣቶች ነው፡፡ ዶ/ር ሚካኤል እንደሚለውም፣ ስኬቲንግ የታዳጊዎችን አመለካከት ቀና በማድረግ ረገድ ከፍተኛ ሚና ይጫወታል፡፡ ‹‹ስኬቲንግ በራስ መተማመንን በመጨመር ስኬታማ ለመሆን የሚያነሳሳ ነው፤›› ይላል፡፡ ስኬቲንግ ታዳጊዎችና ወጣቶች ራሳቸውን በነፃነት የሚገልጹበት መንገድ ከመፍጠሩ ባሻገር ጥሩ መዝናኛ እንደሆነም ይናገራል፡፡

ላፍቶ ሞል ጀርባ በሚገኘው ወረዳ 3 የወጣቶች ማዕከል አካባቢ ከመንግሥት በተሰጣቸው ቦታ የተገነባው አዲስ ስኬት ፓርክ፣ ከተለያዩ አካባቢዎች ለተውጣጡ ስኬተሮች አገልግሎት ይሰጣል፡፡ ስኬት ቦርዶች፣ የደኅንነት ዕቃዎችና ሌሎችም ለስፖርቱ የሚያስፈልጉ ቁሳቁሶችም በፓርኩ ይገኛሉ፡፡  

ማኅበረሰቡ ስለ ስኬቲንግ ያለው አመለካከት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻለ እንደመጣ የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያው ይናገራል፡፡ ፓርኩ መኖሩ ደግሞ አሁን ካለው የተሻለ የግንዛቤ ለውጥ እንደሚያመጣ ተስፋ ያደርጋሉ፡፡ በተለያዩ የክልል ከተሞች የስኬት ፓርኮች የመገንባት ዕቅድም አላቸው፡፡ ‹‹ስኬቲንግ በጀመርንበት ወቅት መንገድ ላይ የሚያስቆሙንና ስኬት ቦርዳችንን የሚቀሙን ሰዎች ነበሩ፤ አሁን አመለካከቱ እየተለወጠ ነው፡፡ መንገድ ላይ ስኬት ስናደርግ ሰዎች ተሰብስበው ያዩናል እንጂ አይከለክሉንም፡፡ ልጆቻቸውን እንድናሠለጥንላቸው የሚጠይቁን ወላጆችም እየበዙ ነው፡፡ አሁን የስኬተሮች ችሎታም እየተሻሻለ ነው፤›› ይላል፡፡

በተለያዩ የክልል ከተሞች ስኬት ፓርክ የማስገንባት ህልማቸው ዕውን ሲሆን፣  የስኬተሮች ቁጥር የበለጠ እንደሚጨ ያምናል፡፡ ስኬቲንግ ጥንቃቄ ካልተወሰደ ለጉዳት ሊያጋልጥ ይችላል፡፡ ለስኬቲንግ ባልተዘጋጁ ቦታዎች ስኬት ማድረግ ደግሞ ጉዳቱን ሊያከፋው ይችላል፡፡ ፓርኩ ለስኬቲንግ ምቹ የሆኑና ደኅንነታቸው የተጠበቀ የቦርድ ማንሸራተቻዎች ያሉት መሆኑ ጉዳት እንዳይኖር ይናገራል፡፡ ስኬቲንግ ከመዝናኛነቱ ጎን ለጎን ስፖርታዊ እንቅስቃሴም በመሆኑ፣ በኦሊምፒክ ውድድሮች ይካተታል፡፡ በውድድሩ የሚሳተፉና ጥሩ ውጤት የሚያስመዘግቡ ወጣቶች እንዲበራከቱም ስኬት ፓርኮች በየከተማው ቢከፈቱ መልካም ነው ይላል ዶ/ር ሚካኤል፡፡

 

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ለሲኒመር ትሬዲንግ አ/ማ አባላት በሙሉ የጠቅላላ ጉባኤ የስብሰባ ጥሪ

ለሲኒመር ትሬዲንግ አ/ማ አባላት በሙሉ የጠቅላላ ጉባኤ የስብሰባ ጥሪ ሲኒመር ትሬዲንግ...

የባህር በር በቀጣናዊ ተዛምዶ ውስጥ

በበቀለ ሹሜ መግቢያ በ2010 ዓ.ም. መጋቢት ማለቂያን ይዞ ዓብይ አህመድ በጠቅላይ...

ሥጋት ያስቀራል ተብሎ የሚታሰበው የጫኝና አውራጅ መመርያ

በአዲስ አበባ ከተማ በሕገወጥ መልኩ በመደራጀት ማኅበረሰቡ ላይ እንግልትና...

ማወቅ ወይስ አለማወቅ – ድፍረት ወይስ ፍርኃት?

በአሰፋ አደፍርስ ወገኖቼ ፈርተንም ደፍረንም የትም አንደርስምና ለአገራችን ሰላምና ክብር...