የብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን (ሜቴክ) በቅርቡ ከዚህ ዓለም ለተለዩት ኢንጂነር ስመኘው በቀለ ቤተሰቦች የሚውል የ800 ሺሕ ብር ድጋፍ ለማድረግ መወሰኑን አስታወቀ፡፡
በኮርፖሬሽኑ የሕዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሚካኤል ደስታ ተፈርሞና የተቋሙ ማኅተም አርፎበት የወጣው መግለጫ፣ ‹‹የልማት አርበኛው ኢንጂነር ስመኘው በቀለ በታላቁ ህዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ግንባታ አንዱ ኮንትራክተር ለሆነው ተቋማችን ትልቅ አጋዥ የነበሩ የአገር ሀብትና ባለውለታ ሕልፈት፣ የወላጆችና የቤተሰቦቻቸውን ሕይወትም አደጋ ላይ የጣለ መሆኑን ተቋማችን ይገነበዛል፤›› ብሏል፡፡
‹‹ለአቅመ ደካማ አባታቸው 200 ሺሕ ብር በባንክ ሒሳብ ቁጥራቸው እንዲገባ፣ ለልጆቻቸውና ለባለቤታቸው 600 ሺሕ ብር በባንክ ሒሳብ ቁጥራቸው እንዲገባ፣ በድምሩ 800 ሺሕ ብር እንዲሰጣቸው፤›› እንደሚደረግ ኮርፖሬሽኑ አስታውቋል፡፡
ሪፖርተር ባደረገው ማጣራትም ገንዘቡ በማንኛውም ወቅት ከኮርፖሬሽኑ ወጪ እንዲደረግ መዘጋጀቱን፣ ሆኖም በኢንጂነሩ ልጆች ወይም በአባታቸው ስም የተከፈተ የባንክ ሒሳብ እስኪቀርብለት እየተጠባበቀ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡
በተያያዘ ዜና የትግራይ ክልል ምክትል ፕሬዚዳንት ደብረ ጽዮን ገብረ ሚካኤል (ዶ/ር) ለኢንጂነር ስመኘው ልጆች አስፈላጊውን ድጋፍ የክልሉ መንግሥት እንደሚያደርግ፣ ቅዳሜ ሐምሌ 21 ቀን 2010 ዓ.ም. በመቀሌ ስታዲየም በታከሄደው ሕዝባዊ ሰልፍ ወቅት አስታውቀዋል፡፡
እንቆቅልሹ እስካሁንም ያልታወቀው የኢንጂነር ስመኘው አሟሟት ለመላው ኢትዮጵያውያን ከባድ ሐዘን ትቶ ማለፉ ይታወቃል፡፡ ሐምሌ 19 ቀን 2010 ዓ.ም. መስቀል አደባባይ አካባቢ በመኪናቸው ውስጥ በጥይት ተመትተው ሞተው የተገኙት ኢንጂነር ስመኘው፣ የቀብር ሥርዓታቸው በታላቅ ክብር እሑድ ሐምሌ 22 ቀን 2010 ዓ.ም. በመንበረ ፀባኦት በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል፡፡ የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን የኢንጂነሩን አሟሟት እያጣራ እንደሚገኝ ከመግለጹ በቀር፣ እስካሁን ስለአሟሟታቸው የሚያስረዳ የተጨበጠ መረጃ አልተገኘም፡፡