ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) በመጪው መስከረም ወር 2011 ዓ.ም. አላስፈላጊ ናቸው የሚሏቸውን አንዳንድ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶችን እንደሚያጥፉ አስታወቁ። በአሜሪካ ከሚገኙ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር ተገናኝተው በወቅታዊ የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ የተወያዩት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ፣ አሁን ባለው የካቢኔ አወቃቀር ፋይዳ የሌላቸው ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች መኖራቸውን ገልጸዋል።
በየትኛውም አገር ከ30 በላይ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶችን አዋቅሮ የሚሠራ መንግሥት አለመኖሩን የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በኢትዮጵያ ሁኔታ ደግሞ ለወጪ የሚዳርጉ ከመሆናቸውም በላይ፣ የሥራ ድርሻ መጣረስ ከመፍጠር ውጪ ፋይዳ እንደሌላቸው ገልጸዋል። በመሆኑም በመጪው መስከረም ወር ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶችን እንደሚያጥፉ በይፋ ተናግረዋል።
በአሁኑ ወቅት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በእረፍት ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ የቀጣዩ ዓመት የሥራ ዘመኑን በመስከረም ወር የመጨረሻ ሳምንት ይጀምራል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይፋ ባደረጉት ዕቅድ መሠረትም ፓርላማው የቀጣይ ዓመት የሥራ ዘመኑን የሚጀምረው ሥራ አስፈጻሚውን መንግሥት መልሶ በማደራጀት ይሆናል።
አፋኝ የተባሉ ሕጎችን ለማሻሻል ግብረ ኃይል ተቋቁሞ እየተሠራ መሆኑን አውስተው፣ እስከሚቀጥለው ዓመት መግቢያ ድረስ ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ ሥራዎችን የማጠናቀቅ ተግባር እንደሚከናወንም ተናግረዋል። የበጎ አድራጎትና ማኅበራት አዋጅ፣ የፕሬስና የመረጃ ነፃነትና የፀረ ሽብርተኝነት ሕጉ ማሻሻያ ከሚደረግባቸው መካከል መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ የፀረ ሽብርተኝነት ሕጉን በተመለከተ ግን አስተሳሰብ እስካለ ድረስ የፀረ ሽብር ሕጉ ማሻሻያ ተደርጎበት እንደሚቀጥል፣ ነገር ግን በፀረ ሽብርተኝነት ሕግ ስም ጤነኛውን አስሮ የማሸበር ተግባር ሊጠፋ እንደሚገባ ተናግረዋል።
ዋነኛ ዓላማቸውም ከሁለት ዓመት በኃላ የሚደረገው ምርጫ ዴሞክራሲያዊና ሰላማዊ ማድረግ መሆኑንና ይኼንንም እንደሚወጡ እርግጠኛ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡