ኢዴፓ ከኢራፓና ከሰማያዊ ፓርቲ ጋር ጥምረት ለመፍጠር እየመከረ ነው
አምስት ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ለመጀመርያ ጊዜ ገዥውን ፓርቲ ጨምሮ በአገር አቀፍ ደረጃ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ድርጅቶች የሚሳተፉበት፣ አገራዊ የዕርቅና የመግባባት ኮንፈረንስ በነሐሴ ወር መጨረሻ ለመጥራት ዝግጅት እያደረጉ መሆኑ ታወቀ፡፡
በነሐሴ ወር መጨረሻ ይካሄዳል የተባለውን ኮንፈረንስ በጋራ ዝግጅት የጀመሩት የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ)፣ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ)፣ ሰማያዊ ፓርቲ፣ የኢትዮጵያ ራዕይ ፓርቲ (ኢራፓ) እና የኦሞ ሕዝብ ድርጅት መሆናቸውን ከአዘጋጆቹ ለማወቅ ተችሏል፡፡
የኢዴፓ የጥናትና ምርምር ክፍል ኃላፊ አቶ ዋሲሁን ተስፋዬ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ኮንፈረንሱ በወቅታዊ የአገሪቱ የፖለቲካና የዴሞክራሲ እንቅስቃሴ ሁኔታ በጋራ ለመምከር፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች እንዴት በጋራ መሥራት እንደሚችሉ ውይይትና ምክክር ለማድረግ ነው፡፡
ኮንፈረንሱ በብሔራዊ መግባባትና በብሔራዊ ዕርቅ ላይ እንደሚያተኩርም ገልጸዋል፡፡ ኮንፈረንሱ ሁሉን አቀፍ መድረክ እንዲሆን ታስቦበት ስለሚከናወን፣ መንግሥትን ጨምሮ (ገዥው ፓርቲ ኢሕአዴግ) ሁሉም ተቃዋሚ ፓርቲዎች በአገር ውስጥ ያሉትም ሆኑ ከውጭ ይገባሉ የሚባሉት አርበኞች ግንቦት ሰባትና ሌሎችም እንደሚሳተፉ አቶ ዋሲሁን አስረድተዋል፡፡ ብሔራዊ ዕርቅ ማድረግ በሚቻልበት ሁኔታ ላይም ይመከራል ሲሉም አክለዋል፡፡
በጉባዔው ላይ የሚሳተፉ ድርጅቶች ተቀራራቢነት ያላቸውና ተዛማጅ አቋም የሚያራምዱ በጋራ (በጥምረትም ይሁን በውህደት)፣ ድርጅት መመሥረት የሚችሉም ካሉ የውይይት መንገድ ይከፈታል በማለት አስረድተዋል፡፡
ከፖለቲካ ድርጅቶች አንዳንዶቹ ቀደም ብለው ውህደት ለማድረግ ወይም የጋራ ጥምረት ለመፍጠር የጀመሩ መሆናቸውን ያወሱት አቶ ዋሲሁን፣ በሚዘጋጀው አገር አቀፍ ኮንፍረንስ በርካታ ድርጅቶች በጋራ ለመሥራትና ለመታገል የሚያስችል ትብብር ሊፈጥሩ እንደሚችሉም እምነታቸውን ገልጸዋል፡፡
በተናጠል ያሉ እንቅስቃሴዎችን በተመለከተም ድርጅታቸው ኢዴፓ በጋራ ለመታገል ከሰማያዊ ፓርቲና ከኢራፓ ጋር ምክክር መጀመሩ ለአብነት በመጥቀስ አስረድተዋል፡፡
በሦስቱ ድርጅቶች የተጀመረው ውይይት የቀጠለ መሆኑን ያስረዱት አቶ ዋሲሁን፣ ውህደት ወይም ቅንጅት ወይም ግንባር ለመፍጠር ስምምነት ላይ አለመደረሱን ጠቁመዋል፡፡ ነገር ግን በቅርቡ አንድ ውሳኔ ላይ እንደሚደረስ ግምታቸውን ገልጸዋል፡፡
በተመሳሳይ ሰማያዊ ፓርቲ ቀደም ብሎ ውህደት መፍጠር ወይም በጋራ ለመታገል ፍላጎት እንዳለው ያረጋገጠ ሲሆን፣ በቅርቡ ወደ አገር ቤት ይገባል ተብሎ ከሚጠበቀው የአርበኞች ግንቦት ሰባት አመራር ጋር በጋራ የእንሥራ ጥያቄ ለማቅረብ ፍላጎት እንዳለው የፓርቲው አመራሮች ገልጸዋል፡፡
በአገር ውስጥ ያሉትም ሆነ በውጭ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ድርጅቶች በጋራ ከመሥራት ይልቅ በተናጠል የሚንቀሳቀሱ ስለሆነ፣ በጋራ እንታገላለን ካሉ በኋላ በአመራሮች አለመግባባት ሲከፋፈሉ ይስተዋላል፡፡
የፖለቲካ ተንታኞች እንደሚሉት ይህ አካሄዳቸው ፓርቲዎችን ደካማ እንዲሆኑ ከማድረጉ ባሻገር፣ ደጋፊዎቻቸውን እምነት ማሳጣታቸው ብዙ ጊዜ ይነገራል፡፡
ይኼንን ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) በቅርቡ በአሜሪካ ባደረጉት ጉብኝት በውጭ ካሉ የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር ባደረጉት ውይይት ገልጸውታል፡፡
በተለይ በዋሽንግተን ዲሲ ከፖለቲካ ድርጅቶች አመራሮች ጋር ሲወያዩ፣ ከሌሎች ተመሳሳይነት ካላቸው ድርጅቶች ጋር በመዋሀድ ወይም በመጣመር ጠንካራ ድርጅት መሥርተው በዴሞክራሲያዊ መንገድ ቢታገሉ፣ ለአገሪቱ ዴሞክራሲ ገንቢ አስተዋፅኦ ማድረግ እንደሚችሉ ምክራቸውን ለግሰው ነበር፡፡
በአገር ቤት ውስጥ ብቻ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ተመዝግበው የሚታወቁ የፖለቲካ ድርጅቶች ከ70 በላይ እንደሚሆኑ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ በውል ባይታወቅም በውጭ አገር ሆነው እንታገላለን የሚሉ የፖለቲካ ድርጅቶችም በርካታ ቁጥር እንዳላቸው ይነገራል፡፡
በዋሽንግተኑ የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ የመጀመርያ ዙር ጉብኝት ብቻ ከ26 በላይ የፖለቲካ ድርጅቶች ተወካዮች እንደተገኙ ተገልጿል፡፡ እነዚህ የፖለቲካ ድርጅቶች በአሜሪካ ብቻ ከሚንቀሳቀሱት ውስጥ ሲሆኑ፣ በሌሎች የአውሮፓና የአፍሪካ አገሮች ተቀማጭነታቸውን ያደረጉ የፖለቲካ ድርጅቶች እኛም አለን ሲሉ ይሰማሉ፡፡