ኮተቤ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ አቅራቢያ ያለው ሙዳይ የሕፃናት፣ ሴቶችና አካል ጉዳተኞች መርጃ ማኅበር ቅጥር ግቢ ሲደርሱ በርካታ ባህላዊ የቤት ውስጥ መገልገያዎች ይመለከታሉ፡፡ መገልገያዎቹ የቀረቡት ለዕይታ ሳይሆን ወደ ማኅበሩ የሚያመሩ ግለሰቦችን ለመፈተን ነበር፡፡ ማበጠር፣ መውቀጥ፣ መፍጨት፣ ጥጥ መፍተልና እበት መጠፍጠፍ ለጎብኝዎች ከሚሰጡት ፈተናዎች መካከል ናቸው፡፡
ማኅበሩ ከሚያዝያ 10 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ‹‹የፍቅር ሳምንት›› በሚል ለአንድ ሳምንት በተለያየ ሙያ የተሰማሩ ግለሰቦችን ጋብዟል፡፡ የመንግሥት ባለሥልጣኖች፣ ሙዚቀኞች፣ ኮሜዲያኖች፣ ጋዜጠኞች፣ ስፖርተኞች፣ ሲቪል ሠራተኞችና የሃይማኖት አባቶች በተለያዩ ቀናት ድርጅቱን እንዲጎበኙ ተጋብዘው ነበር፡፡
በኢትዮጵያውያን ዘንድ የተለመዱና ከጊዜ ወደ ጊዜ በገጠራማ አካባቢዎች ብቻ የተወሰኑ ሥራዎች ለጎብኚዎች ለፈተና የቀረቡበትን ምክንያት የማኅበሩ መሥራችና ዋና ሥራ አስኪያጅ ወ/ሮ ሙዳይ ምትኩ ስታብራራ፣ ‹‹ከተማ ቀመስ ስንሆን የተረሱ ነገሮችን ለማስታወስ አስበን ነው፤›› ትላለች፡፡ ማኅበሩ የሚያሳድጋቸው ሕፃናትም ባህሉን እንዲያውቁ ከማድረግ በተጨማሪ በተለያየ ሙያ ያሉ ሰዎችስ ምን ያህል ሥራዎቹን ይወጧቸዋል? የሚለውን እንደፈተሹ ትገልጻለች፡፡
ማኅበሩ ዘንድሮ ለሁለተኛ ጊዜ ያዘጋጀው ‹‹የፍቅር ሳምንት›› በማኅበሩ የሚረዱ ሴቶች የሚሠሯቸውን ሥራዎች ያስተዋወቀበትም ነው፡፡ የሸክላ ቁሳቁሶች፣ የአገር ባህል ልብሶችና ጌጣ ጌጦች ለዕይታና ለሽያጭ ያቀርባሉ፡፡ በተጨማሪም በተለያየ ሙያ የተሰማሩ ሰዎች ሙዚቃና ሥዕልን የመሰሉ ጥበባዊ ሥራዎችን እንዲሞክሩ ይደረጋሉ፡፡ ባህላዊ ሙዚቃ መሣሪያዎች መጫወትና ገበጣ መጫወትም የዝግጅቱ አካል ናቸው፡፡
ለጋዜጠኞች በተሰጠው ዕለት ቦታውን ስንጎበኝ በኮሜዲያኖች የተሣሉ ሥዕሎች ለዕይታ ቀርበው ነበር፡፡ ወ/ሮ ሙዳይ እንደምትለው፣ ‹‹የፍቅር ሳምንት›› በተለያየ ሙያ ያሉ ሰዎች በማኅበሩ ከሚኖሩ ሕፃናት ጋር ትስስር እንዲፈጥሩ ያለመ ነው፡፡
የዕርዳታ ሲባል ሁልጊዜ ከቁሳዊ ዕርዳታ ጋር ሲያያዝ እንደሚስተዋልና ሰዎች ባላቸው ነገር እንዲተባበሩ ማድረግ እንደሚያስፈልግም ትናገራለች፡፡ በተለያዩ ሙያ ላሉ ግለሰቦች የተለያየ ቀን የተሰጣቸው በተሰማሩበት ሥራ ሰዎችን የሚረዱበት መንገድ እንዳለ ለማሳወቅ በማሰብ እንደሆነም አክላለች፡፡
በማኅበሩ ግቢ ውስጥ ቡና ተፈልቶ፣ ጠላ ተጠምቆ፣ አነባበሮ ተጋግሮና ሌሎችም መሰናዶች ተዘጋጅተው ባህላዊ ይዘት ለማላበስ ሞክረዋል፡፡ ዝግጀቱ ፋሲካ ጥቂት ቀናት ሲቀሩት የሚካሄድ በመሆኑ ለበዓል ለሚያደርጉት መሰናዶ ገቢ ማሰባሰቢያ ይሆናል፡፡ ‹‹ሰው እየተዝናና ለልጆች ፍቅር እንዲሰጥና ባለው ነገር እንዲረዳ ለማድረግ ሞክረናል፤›› ትላለች፡፡
ዓምና በተካሄደው የፍቅር ሳምንት ተጋባዦች ከመዝናናታቸው ባለፈ ማኅበሩ የተረዳበትም አጋጣሚ ተፈጥሮ ነበር፡፡ በተገኘው ዕርዳታ የፋሲካ በዓል ደምቆ ተከብሯል፡፡ ወ/ሮ ሙዳይ ለዘንድሮው የፋሲካ በዓልም ሰዎች በማኅበሩ ተገኝተው ከሕፃናቱ ጋር በዓልን እንዲያሳልፉ ጥሪ አቅርባለች፡፡ በማኅበሩ ሕፃናትና ታዳጊዎችን ጨምሮ 880 ሴቶች ይረዳሉ፡፡