ለአዲስ አበባ ኢሕአዴግ ጽሕፈት ቤት አዲስ ኃላፊ ተሾመ
ላለፉት አሥር ዓመታት በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቁልፍ ቦታዎችን ይዘው ሲመሩ የቆዩት አቶ ተወልደ ገብረ ፃድቃንና አቶ ኃይሌ ፍሰሐ ከሥልጣናቸው ተነሱ፡፡
አቶ ተወልደ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሕዝብ ግንኙነት ዋና አማካሪ፣ እንዲሁም በከተማው ሙሉ ሥልጣን ያለው የአዲስ አበባ ኢሕአዴግ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሆነው ሲሠሩ ቆይተዋል፡፡
አቶ ኃይሌ ፍሰሐ ደግሞ አቶ መኩሪያ ኃይሌ ወደ ፌዴራል መንግሥት የቤቶች ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር ሚኒስትር ሆነው ከተሾሙ ጊዜ ጀምሮ፣ የከተማው ዋና ሥራ አስኪያጅ ሆነው ሠርተዋል፡፡
አቶ ኃይሌ እስካሁን የከተማው ዋና ሥራ አስኪያጅ ሆነው ሲሠሩ የቆዩ ቢሆንም፣ በአዲሱ የአቶ ታከለ ኡማ (ኢንጂነር) ካቢኔ ውስጥ ሳይካተቱ ቀርተዋል፡፡
አቶ ታከለ በሁለቱ ቁልፍ ቦታዎች ላይ አዲስ ሹመት ሰጥተዋል፡፡ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሕዝብ ግንኙነት ዋና አማካሪ ሆነው ከደቡብ ክልል ወደ አዲስ አበባ የመጡት አቶ ተስፋዬ ቤልጂጌ ናቸው የተሾሙት፡፡
አቶ ተስፋዬ የደኢሕዴን ጽሕፈት ቤት ኃላፊ የነበሩ ሲሆን፣ አሁን በአስተዳደሩ መዋቅር የሕዝብ ግንኙነት አማካሪ ሆነው፣ በድርጅት መዋቅር ደግሞ የአዲስ አበባ ኢሕአዴግ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሆነው ተሾመዋል፡፡
ከዚህ ባለፈም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ውኃና ፍሳሽ ባለሥልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት አቶ አወቀ ኃይለማርያም (ኢንጂነር) አቶ ኃይሌን በመተካት የአዲስ አበበ ከተማ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሆነው ተሹመዋል፡፡ አቶ አወቀ ወደ ውኃና ፍሳሽ ባለሥልጣን ከመምጣታቸው በፊት የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ሥራ አስኪያጅ ሆነው ሠርተዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም ምክትል ከንቲባ ታከለ ሁለት ተጨማሪ ሹመቶች ሰጥተዋል፡፡ አንደኛው የአዲስ አበባ ውኃና ፍሳሽ ባለሥልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ ሆነው የተሾሙት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት አቶ ዘሪሁን አባተ፣ የአዲስ አበባ አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣንን በዋና ሥራ አስኪያጅነት እንዲመሩ ደግሞ የኬሚካልና ኮንስትራክሽን ግብዓት ኢንስቲትዩት ኤክስፐርት የሆኑት ወ/ሮ ዓለም አሰፋ ተሹመዋል፡፡