የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለሥልጣንን በዋና ዳይሬክተርነት ሲመሩ በቆዩትና በቅርቡ የኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሆነው በተሾሙት አቶ ሀብታሙ ተገኘ (ኢንጂነር) ምትክ፣ አቶ ሞገስ ጥበበ (ኢንጂነር) ተሾሙ፡፡
ለአንድ ወር ያህል ለኃላፊነቱ ሹመት ሳይሰጥ ቆይቶ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ ታከለ ኡማ (ኢንጂነር) አቶ ሞገስን የከተማው መንገዶች ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አድርገው መሾማቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ አዲሱ ተሿሚም ማክሰኞ ነሐሴ 8 ቀን 2010 ዓ.ም. የሹመት ደብዳቤው ደርሷቸዋል፡፡
አቶ ሞገስ ይህንን ኃላፊነት ከመረከባቸው ቀደም ብሎ፣ በኮንስትራክሽን ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት በዋና ዳይሬክተርነት ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡ ቀደም ብሎም በኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን የኮንትራት አስተዳደርና የምሕንድስና ግዥ ኃላፊ በመሆን ሲያገለግሉም ነበር፡፡
ላለፉት 20 ዓመታት የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለሥልጣንን በመምራት አቶ ሞገስ ሦስተኛው ሰው ናቸው፡፡ ባለሥልጣኑን በመምራት አቶ ፍቃደ ኃይሌ (ኢንጂነር) በቀዳሚነት የሚጠቀሱ ሲሆን፣ ከ16 ዓመታት በላይ መርተውታል፡፡ በአሁኑ ወቅት አቶ ፍቃዱ የሙስና ክስ ተመሥርቶባቸው በእስር ላይ እንደሚገኙ ይታወቃል፡፡ እሳቸውን በመተካት አቶ ሀብታሙ የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ሆነው ሲያገለግሉ ከቆዩ በኋላ፣ በቅርቡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሆነው መሾማቸው ይታወሳል፡፡
አዲሱ ተሿሚ በአዲስ አበባ ከተማ የተጀመሩ ፕሮጀክቶችን በአጭር ጊዜ ማጠናቀቅ፣ በመንገድ መሠረተ ልማት ላይ ያሉ ችግሮችን ለመፍታት የሚያስችሉ አዳዲስ ፕሮጀክቶችን መቅረፅ በቀዳሚነት የሚያከናውኗቸው ተግባራት መሆናቸውን፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤት በማኅበራዊ ድረ ገጹ አስታውቋል፡፡