‹‹አንጋፋ አርበኞቻችን ዛሬ በልጅ ልጆቻቸውና በልጅ-ልጅ ልጆቻቸው እንደሚኮሩ እርግጠኛ ነኝ፡፡ ምክንያቱም አልጣሉዋቸውምና፤ ሁሌም ታላቁን ድል፣ የገናናው ትውልድ በድል የታጀበ የአርበኝነት ተጋድሎን ያስታውሳሉና፡፡››
የሩሲያ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፣ የሶቪየት ኅብረት ቀይ ጦር ከ71 ዓመት በፊት ወራሪውን የናዚ ጀርመን ጦር ድል ያደረገበት ክብረ በዓል፣ በሞስኮ ከተማ ሰኞ ግንቦት 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ሲከበር የተናገሩት፡፡ በ1937 ዓ.ም. ናዚ ጀርመን ድል በሆነችበት የሁለተኛው የዓለም ጦርነት (ከ1933 እስከ 1937 ዓ.ም.) ከዓለም ሕዝብ 80 በመቶው በጦርነቱ ውስጥ የነበረ ሲሆን፣ የ55 ሚሊዮን ሕይወትን ቀጥፏል፡፡ ናዚ ጀርመን ሶቭየት ኅብረትን በሰኔ 1933 ዓ.ም. የወረረች ሲሆን፣ ለአራት ዓመት በዘለቀው ጦርነት 27 ሚሊዮን የሶቪየት ሕዝብ አልቋል፡፡ የሁለተኛውን የዓለም ጦርነት ሩሲያና የቀድሞዎቹ የሶቪየት ሪፐብሊኮች እንደሚገልጹት፣ ‹‹ታላቁ የአርበኝነት ጦርነት›› 71ኛ ክብረ በዓል በሞስኮ ቀይ አደባባይ ሲከበር፣ የሩሲያ ፕሬዚዳንትና የሩሲያ ጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ ቭላድሚር ፑቲን ከሰልፈኞቹ ጋር ተቀላቅለውና የአርበኛውን አባታቸው ፎቶግራፍ ይዘው ከመሰለፋቸው ባሻገር፣ ከ10 ሺሕ የሚበልጡ እግረኛ ወታደሮች፣ ዘመናዊ ታንኮች፣ ኒውኩሌር ማስወንጨፍ የሚችሉ ሚሳይሎችም ተሰልፈዋል፡፡ ‹‹ሱ 35›› (SU35) የተሰኘው ዘመናዊ ተዋጊ ጄትን ጨምሮ የተለያዩ ተዋጊ አውሮፕላኖች የአየር ላይ ልዩ ትርኢት አሳይተዋል፡፡