በፋሺስት ኢጣሊያ ወረራ ጊዜ ከኢትዮጵያ ጎን ሆኖ በአብራሪነትና በአሠልጣኝነት በተሰለፉት አሜሪካዊ ኰሎኔል ጆን ሮቢንሰን ስም የተሰየመ የቴክኖሎጂ ማዕከል አገልግሎት መስጠት ጀመረ፡፡
በብሔራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መጻሕፍት ኤጀንሲ አንደኛው ጥግ ውስጥ በአሜሪካ ኤምባሲ ትብብር የተሠራው ማዕከል ከ10 ሚሊዮን ብር በላይ የወጣበት ሲሆን፣ በተለይ ለተማሪዎችና ተመራማሪዎች ዘርፈ ብዙ አገልግሎት ይሰጣል፡፡
ግንቦት 1 ቀን 2008 ዓ.ም. በተካሄደው የምርቃት ሥነ ሥርዓት ላይ ማዕከሉን ያስጎበኙት የአሜሪካ ኤምባሲ መረጃ ማዕከል ዳይሬክተር አቶ ተክለሚካኤል ተፈራ እንደተናገሩት፣ የማዕከሉ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ መገልገያዎች ለብዙ ተማሪዎችና ተመራማሪዎች ጠቀሜታ ይኖራቸዋል፡፡
በማዕከሉ ውስጥ ዓይነ ስውራን መጻሕፍት ለማንበብ የሚገለገሉበት ሳራ ስካነር ሪደር የተሰኘ መሣሪያ አለ፡፡ ለቪዲዮ ፕሮዳክሽን የሚሆን ግሪን ስክሪን ኪት፣ ስሪዲ ፕሪንተርና ዲጂታል ቪዲዮ ኮንፈረንስም (ዲቪሲ) ይገኛል፡፡ በስሪዲ ፕሪንተሩ የቁሳቁሶች ሞዴሎችን አስመስሎ በመሥራት ለተለያየ አገልግሎት ማዋል ይቻላል፡፡ ለሕክምና፣ ለዲዛይንና ለሌላም ሙያ ይጠቅማል፡፡ በዲቪሲው በተለያዩ አገሮች የሚካሄዱ ስብሰባዎችን ወይም ትምህርት መከታተል ይቻላል፡፡
በማዕከሉ ፕሮግራም እየተጻፈላቸው የሚንቀሳቀሱ አነስተኛ ሮቦቶች፣ ኮምፒውተሮችና አይፓዶች ይገኛሉ፡፡ የእንግሊዝኛ ቋንቋ ትምህርት ፕሮግራም፣ 190,000 የኤሌክትሮኒክስ መጻሕፍትና 1.5 ሚሊዮን የሚደርሱ የድኅረ ምረቃ ተማሪዎች የምርምር ጽሑፎችም ይገኛሉ፡፡
ዳይሬክተሩ አያይዘው እንደተናገሩት፣ መሣሪያዎቹ ለጥናት አጋዥ ከመሆናቸው ባሻገር የቴክኖሎጂ ምርምሮችን ያበረታታሉ፡፡ በኢትዮጵያና በአሜሪካ መካከል ያለውን ወዳጅነት ለማመለከትም በጥቁር አሜሪካዊው አውሮፕላን አብራሪ ኰሎኔል ጆን ሮቢንሰን ተሰይሟል፡፡
ኰሎኔል ጆን ሮቢንሰን ፋሺስት ኢጣሊያ ኢትዮጵያን በወረረበት ወቅት ተዋጊ አውሮፕላን በማብረርና ኢትዮጵያውያንን በማሠልጠንም ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክተዋል፡፡ በኢትዮጵያ አየር መንገድ ምሥረታና በጦርነቱ ወቅት የተጫወቱትን ሚና ለማስታወስም በአየር መንገዱ ሐውልት ቆሞላቸዋል፡፡ የተቀበሩትም እዚሁ ኢትዮጵያ ነው፡፡
በዓለም ዙሪያ 700 ተመሳሳይ የአሜሪካ ማዕከሎች ያሉ ሲሆን፣ ከእነዚህ 100ዎቹ በአፍሪካ ይገኛሉ፡፡ የአሜሪካ ኤምባሲ የቴክኖሎጂ ማዕከሎች በባህር ዳር፣ ጅማ፣ ድሬዳዋና አዲስ አበባ በሚገኘው የኤምባሲው ቅጥር ግቢም ይገኛሉ፡፡
የብሔራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መጻሕፍት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ አብርሃም ጮሻ፣ ማዕከሉ መጻሕፍትና ጥናቶችን በሶፍት ኮፒ ማግኘት ለሚፈልጉ ሰዎች ከፍተኛ ጠቀሜታ ይኖረዋል ብለዋል፡፡ የቤተ መጻሕፍቱን አገልግሎት ለማስፋት የሕፃናት ቤተ መጻሕፍት እያስገነቡ ሲሆን፣ የማዕከሉ መኖር ቤተ መጻሕፍቱ የሚሰጠውን አገልግሎት እንደሚያጠናክር ተናግረዋል፡፡ በማዕከሉ ያሉት የኤሌክትሮኒክስ መሣሪያዎች ፈጠራን ከማበረታታታቸው ባሻገር የመሣሪያ አለመኖር በተመራማሪዎች ጥናት ላይ የፈጠረውን ክፍተት እንደሚሞላ አክለዋል፡፡
በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ፓትሪሽያ ሀስላክ፣ ማዕከሉ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ከሚያበረክተው አስተዋጽኦ በተጨማሪ፣ ለባህልና ልምድ ልውውጥ ምቹ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ ‹‹ማዕከሉ ትኩረቱን ያደረገው በወጣቶች ላይ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን የፈጠራ ባህላቸውንና መንፈሳቸውን የሚያዳብሩበት ቦታ ነው፤›› ብለዋል፡፡
የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትሯ ኢንጂነር አይሻ መሐመድ፣ ቤተ መጻሕፍቱ የአገሪቱን ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ባህላዊ እሴቶች የሚያሳዩ መዛግብትን በመጠበቅ፣ ለጥናትና ምርምር ክፍት በማድረግና ከትውልድ ወደ ትውልድ በማሸጋገር እያደረገ ላለው እንቅስቃሴ ማዕከሉ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ብለዋል፡፡