– የበርበራን ወደብ ለማልማት ዲፒ ወርልድ መምጣቱን መንግሥት በመልካም ጎኑ እንደሚቀበለው ገለጸ
የሱዳን የፐብሊክ ዲፕሎማሲ አባላት በአዲስ አበባ በነበራቸው ቆይታ ወቅት፣ ከንግዱ ማኅበረሰብ ጋር በተካሄደ ስብሰባ ሱዳን 30 በመቶ የኢትዮጵያ የወጪና ገቢ ዕቃዎችን የማስተናገድ ፍላጎት እንዳላት አስታወቀች፡፡
የኢትዮ-ሱዳን የቢዝነስ ፎረም ፕሬዚዳንት ወጂድ ሚራንጋኒ እንዳስታወቁት፣ ፖርት ሱዳን ከጁቡቲ ወደብ የበለጠ ስፋትና በአንድ ጊዜ በመቶ የሚቆጠሩ መርከቦችን የማተናገድ አቅም ስላለው ለኢትዮጵያ ምቹ ነው፡፡ ሚራንጋኒ ለሪፖርተር በሰጡት ማብራሪያም ፖርት ሱዳን ከጂቡቲ ወደብ ይልቅ የመርከብ፣ የተቀላጠፈና ርካሽ የትራንዚት አገለግሎት የመስጠት ብቃት አለው ብለዋል፡፡
በአንድ ጊዜ ከ100 ያላነሱ የኢትዮጵያ መርኮች ሳይጨናነቁ በሱዳን ወደብ መስተናገድ እንደሚችሉና መንግሥታቸውም ለኢትዮጵያ በዋጋ ቅናሽ የወደብ አገልግሎት ለመስጠት ዝግጁ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በማዳበሪያ፣ በብረት፣ በዘይት እንዲሁም በሌሎች ትልልቅ ብትን ጭነቶች መስክ ለኢትዮጵያ የወደብ አገልግሎት ለመስጠት ፍላጎት ከማሳየት በተጨማሪ፣ ከመንግሥት ባለሥልጣናት ጋር ንግግር ተጀምሮ እንደነበርም ሚራንጋኒ ጠቅሰዋል፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥት አንድ ጊዜ ብቻ የአንድ መርከብ ጭነት በሱዳን ወደብ በኩል ካስተናገደ በኋላ፣ እስካሁን ሌላ አገልግሎት እንዳልጠየቀ ሚራንጋኒ ገልጸዋል፡፡ ባለፈው ዓመት 50 ሺሕ ቶን ማዳበሪያ በሱዳን ወደብ በኩል ወደ ኢትዮጵያ መግባቱ ይታወሳል፡፡
ሱዳን ባቀረበችው የአገልግሎት ልስጥ ጥያቄ ላይ ለሪፖርተር ማብራሪያ የሰጡት የማሪታይም ጉዳዮች ባለሥልጣና ዋና ዳይሬክተር አቶ መኮንን አበራ፣ በሱዳን ወደብ ዕቃዎችን ለማስገባት የትራንስፖርት ወጪውና ርቀቱ ሊታይ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም 30 በመቶ የሱዳን ወደብን ለመጠቀም መጀመሪያ አስመጪዎችና ላኪዎች በወደቡ አዋጪነት ላይ የሚኖራቸው ፍላጎት ሊተኮርበት እንደሚገባ አስረድተዋል፡፡
የኢትዮ-ሱዳን ቢዝነስ ፎረም ፕሬዚዳንት ሱዳን ለኢትዮጵያ የሰጠችውን ባንክ የመክፈት ዕድል፣ ኢትዮጵያም ለሱዳን ባንኮች በመስጠት ቅርንጫፍ እንዲከፍቱ መፍቀድ እንደሚገባት ጠይቀዋል፡፡ በሁለቱ አገሮች መካከል ስምምነት የተደረገበት ዜሮ ታሪፍ አሠራርም ተግባራዊ ይደረግ ዘንድ ሚራንጋኒ አሳስበዋል፡፡
ከዚህ ባሻገር ሱዳን ከምታመርተው ጥጥ ውስጥ የኢትዮጵያ ዓመታዊ ፍላጎት ሙሉ በሙሉ ማሟላት የሚያስችል አቅም ስላላት እንድትገዛ ጥሪ ያቀረቡት ሚራንጋኒ፣ በዓመት ከ130 እስከ 150 ሺሕ ቶን የሚገመት ጥጥ ለኢትዮጵያ የማቅረብ አቅም እንዳላት አስረድተዋል፡፡
በተያያዘ ዜና የዱባዩ ዲፒ ወርልድ የተባለው የወደብ አስተዳዳሪ ኩባንያ፣ የሶማሌላንድን የበርበራ ወደብ ከመንግሥት ጋር አብሮ ለማልማት የ442 ሚሊዮን ዶላር ኢንቨስትመንት እንደሚያካሂድ ይፋ አድርጓል፡፡ ይህንን ተከትሎም መንግሥት የዲፒ ወርልድ በርበራ ወደብን ለማልማት ያሳየው ፍላጎት በኢትዮጵያ በኩል ትልቅ ጥቅም ያለው መሆኑን፣ ኢትዮጵያም የበርበራ ወደብን መጠቀም እስከፈለገች ድረስ መልካም አጋጣሚ መሆኑን አቶ መኮንን ገልጸዋል፡፡
በመላው ዓለም ወደቦችን በማስተዳደር የታወቀው ዲፒ ወርድ በአውሮፓ ግንባር ቀደም መሆኑም ይነገርለታል፡፡ የጂቡቲ ወደብን ጨምሮ ከብራዚል እስከ ቻይና በርካታ ወደቦችን በማስተዳደር ግዙፍ ልምድ ያለው ይህ ኩባንያ፣ የበርበራ ወደብን ለማልማት ከሌሎች ሦስት ኩባንያዎች ጋር ሲፎካከር እንደነበር ይታወሳል፡፡