የተባለ አገር በቀል ድርጅት ከሁለት ዓመታት በፊት ለተቋቋመው የኢትዮጵያ ጠለፋ ዋስትና አክሲዮን ማኅበር፣ የሰው ሀብት ስትራቴጂ ለማዘጋጀት የወጣውን ጨረታ በ2.1 ሚሊዮን ብር አሸነፈ፡፡ ጨረታውን ያሸነፈው ከታዋቂው የሆላንድ ኩባንያ ጋር ተወዳድሮ ነው፡፡
የሚዘጋጀው ስትራቴጂ የጠለፋ ዋስትና አክሲዮን ማኅበሩን አጠቃላይ የሰው ሀብት ስትራቴጂና የሰው ሀብት አስተዳደር እንዲኖረው ያስችላል ተብሏል፡፡
‹‹የዚህን ፕሮጀክት ጠቀሜታ ስለምንረዳ የኩባንያውን ዓላማ እንዲያሳካ ለማስፈጸም እንጥራለን፤›› ሲሉ፣ የኤችኤስቲ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ግዛው ለሪፖርተር በኢሜይል አስታውቀዋል፡፡
ከሦስት እስከ አምስት ዓመታት እንደሚወስድ የሚገመተው የስትራቴጂው ዝግጅት፣ ከተለያዩ ዓለም አቀፍ ተመሳሳይ ድርጅቶች ልምዶች እንደሚቀመሩለትም ለማወቅ ተችሏል፡፡ ስትራቴጂው እ.ኤ.አ. በጥር ወይም በየካቲት 2019 እንደሚጠናቀቅም ታውቋል፡፡
ስትራቴጂውን የሚሠራው ድርጅት ከአሁን ቀደም ከዴሎይት ጋር አጋር የነበረ ሲሆን፣ በአጋርነቱ ወቅት ለኢትዮጵያ መድን ድርጅትና ለአቢሲኒያ ባንክ ተመሳሳይ ፕሮጀክቶችን ተግብሯል፡፡
‹‹እ.ኤ.አ. በ2017 በአፍሪካ ቀዳሚ የጠለፋ ዋስትና ሰጪ ለመሆን ዕቅድ አስቀምጠናል፡፡ ዕቅዳችን ከአፍሪካ አልፎ በመካከለኛውና በሩቅ ምሥራቅ አገሮች መሥራት ስለሆነ፣ በቁጥርም ሆነ በልማት ለዛ ብቁ የሚያደርገን ስትራቴጂ ስለሚያስፈልገን ነው ስትራቴጂውን የምናሠራው፤›› ሲሉ የኢትዮጵያ የጠለፋ ዋስትና ኩባንያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ የወንድወሰን ኢተፋ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
ስለዚህም የጨረታ ሰነዱ የተዘጋጀው ይህንን በማሰብ እንደሆነ ገልጸው፣ በኢትዮጵያ ግመታና የሥጋት መጠን ልኬት የሚሠሩ ባለሙያዎች ከውጭ እንደሚገዙና እንዲህ ያሉ ባለሙያዎችን ኩባንያው ውስጥ ማፍራት ይሻላል ወይስ ከውጭ ቀጥሮ ማሠራት ይሻላል የሚለውን ስትራቴጂው እንደሚጠቁም አስረድተዋል፡፡
‹‹የወደፊቱን የሚመለከት ስትራቴጂ ነው የሚሠራው፡፡ የመንግሥት መመርያዎች ምን ሊሆኑ እንደሚችሉ የሚጠቁም ጭምር ነው፤›› ሲሉም አብራርተዋል፡፡
የኢትዮጵያ ጠለፋ ዋስትና አክሲዮን ማኅበር እ.ኤ.አ. በ2016 ሥራ የጀመረ ሲሆን፣ በኢትዮጵያ የመጀመርያው የኢትዮጵያ የጠለፋ ዋስትና ሰጪ ድርጅት ነው፡፡ የኩባንያው የተመዘገበ ካፒታሉ አንድ ቢሊዮን ብር ሲሆን፣ የተከፈለ ካፒታሉ ደግሞ ግማሽ ቢሊዮን ብር ነው፡፡
የኩባንያው ባለአክሲዮኖች ኢንሹራንስ ኩባንያዎች፣ ባንኮችና ሌሎች ተቋማት ናቸው፡፡ ሰባት ባንኮች፣ አሥራ ሰባት የኢንሹራንስ ኩባንያዎች፣ ስምንት ግለሰቦችና አንድ የሠራተኞች ማኅበር ባለአክሲዮኖችን ያቀፈ ድርጅት ነው፡፡