[ለክቡር ሚኒስትሩ ደላላ ወዳጃቸው ደወለላቸው]
- ክቡር ሚኒስትር በጣም እፈልግዎታለሁ፡፡
- ምን ተገኘ?
- ቁጭ ብለን ማውራት አለብን፡፡
- በምን ጉዳይ?
- የሚገርም ሐሳብ መጥቶልኛል፡፡
- የአንተ ሐሳብ መቼ መቆሚያ አለው?
- ክቡር ሚኒስትር ይኼኛው የሚገርም የቢዝነስ ሐሳብ ነው፡፡
- ሰውዬ ጊዜውን ረሳኸው እንዴ?
- ክቡር ሚኒስትር ከለውጡ ጋር የሚሄድ የቢዝነስ ሐሳብ ነው፡፡
- እየቀለድክ መሆን አለበት?
- የምን ቀልድ ነው ክቡር ሚኒስትር?
- ስማ ካሁን አሁን እስር ቤት ገባን እያልን በምንጨነቅበት ወቅት ሌላ የሌብነት ሐሳብ አምጥተህ ጉድ ልታደርገኝ ነው?
- ክቡር ሚኒስትር በቢዝነሱም ቢሆን እኮ መደመር ያስፈልጋል፡፡
- እኔ ይኼ መደመርና መቀነስ የሚሉት ነገር አይገባኝም፡፡
- ማለቴ ተደምሬያለሁ ምናምን ካሉ እኮ ችግር የለውም፡፡
- ነገርኩህ እኮ ተደመርኩ ስትል ቀንሰውህ ቁጭ ልትል ትችላለህ፡፡
- ክቡር ሚኒስትር የሚገርም የቢዝነስ ሐሳብ እኮ ነው ያለኝ፡፡
- ለመሆኑ ሰሞኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሰጡትን መግለጫ ሰምተኸዋል?
- ምን አሉ?
- ማንም ወንጀለኛ ለዘለዓለም ተደብቆ አይቀርም ብለዋል፡፡
- እሱ ለሚዲያ ፍጆታ ነው የተናገሩት፡፡
- ምን ማለት ነው?
- ያው ባለፈው ጊዜ ዶላር ምናምን የደበቁት ላይ ዕርምጃ እንወስዳለን ብለው በተግባር ግን ተቸግረዋል፡፡
- ምን እያልከኝ ነው?
- አሁን እንደዚያ ይበሉ እንጂ እርስዎ ተነኩ ማለት ከሚያጋልጡዋቸው ሰዎች ብዛት አንፃር ያሉት እስር ቤቶች ሊበቁን አይችሉም፡፡
- ለመሆኑ ምን ዓይነት የቢዝነስ ሐሳብ መጥቶልህ ነው?
- ሰሞኑን ሚዲያ ከተከታተሉ ሐሳቡ በጣም ይገባዎታል፡፡
- እኮ ምንድነው?
- የቴሌ ቢዝነስ ውስጥ እንድንገባ ነው፡፡
- ሰውዬ አሁን እንደለየልህ ነው የገባኝ፡፡
- ምነው ክቡር ሚኒስትር?
- ጠቅላይ ሚኒስትሩ አንድ ኩንታል ሲም ካርድ ተይዟል ሲሉ አልሰማህም?
- ምን ችግር አለው ታዲያ አንዳንዱ ሰው ጤፍ ይበላል፣ ለአንዳንዱ ደግሞ ሲም ካርድ ነው እንጀራው፡፡
- እኔን እዚህ ውስጥ እንዳታስገባኝ፡፡
- ለነገሩ ቢዝነሱ ከቴሌ ጋር የተገናኘ እንጂ የሲም ካርድ አይደለም፡፡
- ስማ ትንሽ ያካበትነው ሀብት በአንዴ ድምጥማጡ እንዲጠፋ ነው?
- ለምን ክቡር ሚኒስትር?
- ቴሌ በከፍተኛ መጠን ታሪፉን ቀንሶ እኛም እንድንከስር ነው የቴሌ ቢዝነስ ውስጥ እንግባ የምትለኝ?
- ምን ነካዎት ክቡር ሚኒስትር?
- አንተ ምን ነካህ ልበል እንጂ?
- ቴሌ ታሪፉ በመቀነሱ እኮ በርካታ ሰው የቴሌ ደንበኛ መሆኑ አይቀርም፡፡
- ያ ታዲያ ለእኛ ምን ይፈይዳል?
- ክቡር ሚኒስትር በዚህ ወቅት የስልክ ገበያ ይደራል፡፡
- እኛ እኮ ከስልክ ቢዝነስ የወጣነው ቴሌ አንድ ሰው ከውጭ ሲመጣ ከአንድ ስልክ በላይ ይዞ መግባት አይችልም ስላለ ነው፡፡
- እሱም መመርያ ተነሳ እኮ፡፡
- ቢነሳስ ከሌሎች ነጋዴዎች ጋር እንዴት መወዳደር እንችላለን?
- ገበያውን ሰብረን የምንገባበትን መንገድማ መቼም አይጠፋዎትም?
- ሒሳብ ቀንሰን እናምጣ እያልከኝ ነው?
- እንደዚያ አልወጣኝም፡፡
- ታዲያ ፎርጂድ ስልክ እንድናመጣ አስበህ ነው?
- የለም የለም፡፡
- እንዴት ነው ታዲያ ገበያውን ሰብረን የምንገባው?
- በኮንትሮባንድ!
[ለክቡር ሚኒስትሩ አንድ ስልክ ከውጭ ተደወለላቸው]
- ሄሎ ክቡር ሚኒስትር?
- ማን ልበል?
- ረስተውኝ ሊሆን ይችላል ድሮ እንተዋወቅ ነበር፡፡
- ይቅርታ አላወቅኩህም?
- ሃይ ስኩል አንድ ላይ ተምረን ነበር፡፡
- ያው ጊዜው ረዥም በመሆኑና በወቅቱም በርካታ ተማሪዎች በመኖራቸው አላስታወስኩህም፡፡
- ለማንኛውም እኔም በትግል ውስጥ ነበርኩ፡፡
- ከእኛ ጋር ጫካ ገብተህ ነበር?
- አይ ከእናንተ በተቃራኒው ጎራ ሆኜ ስታገል ነበርኩ፡፡
- አሁን የት ነው ያለኸው?
- እኔ ከአገር ከወጣሁ ወደ 30 ዓመት እየተጠጋኝ ነው፡፡
- ውጭ አገር ነው ይኼን ያህል ዓመት የታገልከው?
- አዎን ክቡር ሚኒስትር አሁን ግን በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋባዥነት ወደ አገር ቤት ልመለስ ነው፡፡
- ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያውቁሃል እንዴ?
- ማለቴ ዳያስፖራዎች ወደ አገራችሁ ግቡ ባሉት መሠረት ወደ አገር ቤት ለመመለስ አስቤ ነው፡፡
- ስለዚህ እዚህ መጥተህ ሥራ ልትጀምር አስበሃል?
- ሥራውንማ እናንተ ናችሁ የምትሰጡን፣ ከእኔ የሚጠበቀው ወደ አገር ቤት መመለስ ነው፡፡
- ለመሆኑ ውጭ አገር ምንድን ነበር የምትሠራው?
- እኔ ሥራ ወዳድ ስለሆንኩ ምንም ሥራ አልመርጥም፡፡
- በጣም ደስ ይላል፡፡
- አሁን አገሪቱ ውስጥ እየተደረገ ያለውን ለውጥ ለመደገፍ ነው የምመጣው፡፡
- እኛም ሁሌም አገራችንን የሚደግፍልን ዜጋ እንፈልጋለን፡፡
- እኔ ወደ አገር ቤት ከመምጣቴ በፊት ግን ማወቅ የምፈልጋቸው ነገሮች አሉ፡፡
- ምንድነው ማወቅ የምትፈልገው?
- ማለቴ አገር ቤት ከመጣሁ ወደ 30 ዓመታት ሊሆነኝ ስለሆነ፣ ስለአጠቃላይ የአገሪቱ ሁኔታ ማወቅ እፈልጋለሁ፡፡
- መቼም በሚዲያ እንደምትሰማው አገሪቱ በከፍተኛ ዕድገት ላይ ናት፡፡
- እንግዲህ የእኔም አመጣጥ እዚህ ዕድገት ላይ ተጨማሪ ዕድገት ለማምጣት ነው፡፡
- ይቅርታ እዚያ ምንድን ነበር የምሠራው ያልከኝ?
- አብዛኛውን ጊዜዬን በዌልፌር ነበር ያሳለፍኩት፡፡
- እ. . .
- አጋሚውን ባገኘሁባቸው ጊዜያት ደግሞ ከሳህን አጠባ እስከ ታክሲ ሾፌርነት ሠርቻለሁ፡፡
- በእውነት ሥራ አክባሪ ሰው ነህ፡፡
- ለማንኛውም አሁን የደወልኩልዎት አንድ ነገር ሰምቼ ነው፡፡
- ምን ሰምተህ?
- ከውጭ ለሚመጡ ዳያስፖራዎች አቀባበል የሚያደርጉት እርስዎ ነዎት ሲባል ሰምቼ ነው፡፡
- አልገባኝም ምን እያልክ ነው?
- ማለቴ ለእኔም አቀባበል እንዲደረግልኝ ነው፡፡
- ምን ዓይነት አቀባበል?
- ያው በምመጣበት ቀን ኤርፖርት የመንግሥት ልዑክ እንዲጠብቀኝ ነው፡፡
- እሺ?
- በዚያ ላይ እዚያው ኤርፖርት የአገር ውስጥ ሚዲያዎች ተጋብዘው መግለጫ እንድሰጥ ነው፡፡
- ኪኪኪ. . .
- ምን ያስቅዎታል?
- ለመሆኑ ምን ስለሆንክ ነው አቀባበል የሚደረግልህ?
- ሌሎቹ ምን ስለሆኑ ነው አቀባበል የተደረገላቸው?
- እ. . .
- ለማንኛውም ስለኔ አቀባበል ምላሽዎን እፈልጋለሁ፡፡
- አትቀልድ እንጂ ሰውዬ?
- ለነገሩ እኔም አሁን ነው የገባኝ፡፡
- ምኑ ነው የገባህ?
- መንግሥት አቀባበል እንዲያደርግልኝ መጀመርያ መግባት አለብኝ፡፡
- የት ነው የምትገባው?
- ጫካ!
[ክቡር ሚኒስትሩ ከሚስታቸው ጋር እያወሩ ነው]
- አንተ ምንድነው የሰማሁት?
- ምን ሰማሽ ደግሞ?
- ሚዲያ ላይ የሚወራው ሁሉ አሥጊ ነገር ነው፡፡
- ምን ተወራ?
- በርካታ የንግድ ቤቶች እየታሸጉ ነው እኮ፡፡
- ምን ሆነው?
- ጥቁር ገበያ ላይ የተሰማሩ ንግድ ቤቶች እየታሸጉ ነው፡፡
- ምን ትቀልጃለሽ?
- ለነገሩ እኔ በትውውቅ ስለምሠራ ችግር የለውም፡፡
- ቢሆንም መጠንቀቅ አለብሽ፡፡
- አሁን ያሳሰበኝ ሌላ ነገር ነው፡፡
- ምንድነው እሱ?
- አዲሱ ከንቲባ የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ምንም አልተመቸኝም፡፡
- አንቺ ደግሞ አሁን እሳቸው ደሃዎችን ረዱ እንጂ ምን አደረጉ?
- ስለእሱ እኔ ምን አገባኝ?
- ታዲያ ምንድነው የምትይው?
- ከተማ ውስጥ በርካታ ሕንፃዎች አሉ እየተባለ ነው፡፡
- እሱማ ግልጽ ነው፣ ሕንፃዎቹ እኮ የኢኮኖሚው ዕድገት ማሳያ ናቸው፡፡
- አንተ ምንም አልገባህም፡፡
- ምን እያልሽ ነው?
- በሕንፃዎች ላይ አሰሳ እየተደረገ ነው፡፡
- እኛ ታዲያ ምን አገባን?
- ከተማው ውስጥ ከአንድ አይሉ ሦስት ሕንፃዎች እንዳሉን ረሳኸው እንዴ?
- ቢኖሩን ምን ችግር አለው?
- ከየት አምጥተው ሠሩት ተብለን መዋረዳችን አይቀርም፡፡
- ስለእሱ አታስቢ?
- ለምን አላስብም?
- ሕንፃዎቹን እኮ ያለባለቤት ነው የሠራናቸው፡፡
- እሱ አይደል እንዴ እኔን ያሳሰበኝ፡፡
- ምኑ ነው ያሳሰበሽ?
- ከተማዋ ውስጥ ባለቤት የሌላቸው ሕንፃዎች መኖራቸው ተረጋግጧል እያሉ ናቸው፡፡
- እ. . .
- ስማ ያ ሁሉ ሀብት ከንቱ ሊቀር ነው፡፡
- ይኼማ አይሆንም፡፡
- ምናለ ገንዘቡን በዶላር ቀይረን በያዝነው ኖሮ?
- ሴትዮ ልታሳብጂኝ ነው እንዴ?
- እሱማ የተሻለ ነበር፡፡
- እና ተደርሶብናል ነው የምትይው?
- እስካሁን የሚታወቅ ነገር የለም፣ ሕንፃዎቹ ግን ተደርሶባቸዋል፡፡
- ሕንፃዎቹ ምን ሊደረጉ ነው ታዲያ?
- እኔማ መንግሥት እንትን እንዳይለን ነው የፈራሁት፡፡
- ምን እንዳይለን?
- እሟ ቀሊጦ!
[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ የእስር ቤት ኃላፊ ጋ ደወሉ]
- አቤት ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እንዴት ነህ ወዳጄ?
- ዛሬ ከየት ተገኙ ክቡር ሚኒስትር?
- በእውነት በጣም አዝኜ ነው የደወልኩልህ፡፡
- ምነው ክቡር ሚኒስትር?
- እስር ቤታችሁ ውስጥ ይኼን ያህል የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንደሚፈጸም አላውቅም ነበር፡፡
- እንዴት ማለት?
- ይኸው በየሚዲያው ታሳሪዎች የተለያዩ ችግሮች እንደሚገጥማቸው ሲናገሩ ሰምቼ ነው፡፡
- ክቡር ሚኒስትር ታዲያ ይኼ ምን አዲስ ነገር ነው? እርስዎ በሚገባ ጠንቅቀው ያውቁታል፡፡
- ለመሆኑ ታሳሪዎቹ ኢቲቪ ብቻ ነው የሚያዩት?
- ከኢቲቪ ውጪ ሌሎቹን የአገር ውስጥ ሚዲያዎች ያያሉ፡፡
- ስማ ፕሪሚየር ሊግ አያዩም ማለት ነው?
- እ. . .
- ናሽናል ጆግራፊክና ሌሎች ፊልሞችንም አይመለከቱም እያልከኝ ነው?
- ምን ሆነዋል ክቡር ሚኒስትር?
- ቆይ ቆይ ሌላው ቢቀር እስር ቤቱ የተሟላ ፈርኒቸር አለው?
- ምንም አልገባኝም ክቡር ሚኒስትር?
- ማለቴ ታሳሪዎቹ ሶፋ ምናምን አላቸው?
- እየቀለዱ ነው ክቡር ሚኒስትር?
- የእውነቴን ነው እንጂ፡፡
- እኔ እኮ የእስር ቤት ኃላፊ እንጂ የሆቴል ኃላፊ አይደለሁም፡፡
- ስማ አሁን ከለውጡ ጋር መራመድ አለብህ፡፡
- አልገባኝም?
- ምናለበት እስር ቤቱን ሆቴል ብታስመስለው?
- አሁን ነው የገባኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ምኑ ነው የገባህ?
- በቅርቡ ሊመጡ ነው ማለት ነው፡፡
- የት?
- እኛው ጋ!