የሶማሌ ክልል ምክር ቤት የተለያዩ ሹም ሽሮችን አደረገ፡፡ ምክር ቤቱ ሰሞኑን ባደረገው ስብሰባ 27 አመራሮችን የቢሮ ኃላፊ አድርጎ ሾሟል፡፡
ምክር ቤቱ ከሾማቸው አመራሮችም ውስጥ 96 በመቶ የሚሆኑት ከዚህ ቀደም በክልሉ በተለያዩ ኃላፊነቶች የሠሩ ሲሆኑ፣ ቀሪዎቹ ደግሞ አዲሶች መሆናቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡
ከ27 የቢሮ ኃላፊዎች ውስጥ ከምክትል ርዕሰ መስተዳደር ጀምሮ የተለያዩ የቢሮ ኃላፊዎችን ሹመት አፅድቋል፡፡ በዚህም አቶ አደም ፋራህን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አድርጎ ሾሟል፡፡
አቶ አደም ከዚህ ቀደም በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር የኮንስትራክሽን ቢሮ ኃላፊ ነበሩ፡፡ በተጨማሪም ከቀድሞው የክልሉ ፕሬዚዳንት አቶ አብዲ መሀመድ (አብዲ ኢሌ) ጋር በወንጀል ተጠርጥረው በታሰሩ ኃላፊዎች ምትክ አዲስ አመራሮች ተሹመዋል፡፡
ለአብነት የክልሉ የሴቶችና ሕፃናት ቢሮ ኃላፊ በነበሩት ወ/ሮ ራህዋ አህመድ ቦታ፣ ከዚህ ቀደም በቢሮው የዘርፉ ኃላፊ የነበሩት ወ/ሮ ዘይነብ ነጂ ተሹመዋል፡፡
የቀድሞው ፕሬዚዳንት ከሥልጣናቸው ከተነሱ በኋላ ለቀናት የክልሉ ፕሬዚዳንት የነበሩትና በአቶ ሙስጠፋ ዑመር የተተኩት አቶ አህመድ አብዲ፣ የክልሉ ገዥ ፓርቲ ኢሶሕዴፖ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አድርጓቸዋል፡፡
በተመሳሳይ የክልሉ ኮሙዩኑኬሽን ቢሮ ኃላፊ የነበሩት አቶ እድሪስ እስማኤል የኢሶሕዴፓ የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ ሆነው በፓርቲው ተመድበዋል፡፡
በምክር ቤቱ ሹመት ላይ ዳያስፖራዎች እንዲካተቱ ቀርቦ የነበረ ቢሆንም፣ ሕጉ ስለማይፈቅድ ውድቅ መደረጉን ምንጮች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡