ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጀምሮ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤትን እያጥለቀለቀ የሚገኘውን የሕዝብ አቤቱታ በተገቢው መንገድ እንዲፈታ ለተቋቋመው ጽሕፈት ቤት አቶ መኮንን አምባዬ ተሾሙ፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሕዝብ ቅሬታና አቤቱታ ማስተናገጃ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ተክሌ ዱዱ ተነስተው፣ በቅርቡ የቁጠባ ቤቶች ልማት ኢንተርፕራይዝ (40/60) ዋና ዳይሬክተር ተደርገው የተሾሙት አቶ መኮንን ሰኞ ነሐሴ 28 ቀን 2010 ዓ.ም. ተተክተዋል፡፡
አቶ ተክሌ እስካሁን ቦታ ያልተሰጣቸው ሲሆን፣ አቶ መኮንን ደግሞ ምክትላቸው በነበሩት አቶ አፈወርቅ ንጉሡ ተተክተዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ (ኢንጂነር) ሰሞኑን የ40/60 ቤቶችን ተዘዋውረው ጎብኝተው ነበር፡፡ በጉብኝቱ ወቅት የ40/60 ቤቶች ግንባታ ሒደት ከነበረበት ችግር ወጥቶ መስመር መያዙን ገልጸው ነበር፡፡
በወቅቱ የ40/60 ቤቶች ግንባታ ሒደት በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲስተካከል አስተዋጽኦ ላበረከቱት አቶ መኮንን ሌላ ተልዕኮ እንደሚሰጣቸው ገልጸውላቸው ነበር፡፡ በዚህ መሠረት ምክትል ከንቲባው የአስተዳደሩ መዋቅር ከፍተኛ የሆነ የሕዝብ ቅሬታ ቢቀበልም፣ በተገቢው መንገድ እያስተናገደ አይደለም በማለት አቶ ተክሌ እንዲነሱ አድርገው አቶ መኮንንን ሾመዋል፡፡
መረጃዎች እንደሚጠቁሙት በአዲስ አበባ ከንቲባ ሆኖ የሚሾም አመራር ትልልቅ አገራዊ ፕሮጀክቶች ላይ እንዳያተኩር፣ በስትራቴጂና በፖሊሲ ጉዳዮች ጊዜውን እንዳይጠቀም ከሚያደርጉ ጉዳዮች መካከል የሕዝብ ቅሬታዎችና አቤቱታዎች ዋነኛ ናቸው፡፡
በተለይ ከመሬትና መሬት ነክ፣ እንዲሁም ከመኖርያ ቤቶች ጋር የተያያዙ ከይዞታ የማፈናቀል ጉዳዮች ላይ የሚነሱ የሕዝብ ቅሬታዎች በርካታ ናቸው፡፡ የቀድሞው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ድሪባ ኩማ ይህንን መጠነ ሰፊ ችግር ለመፍታት የሕዝብ ቅሬታና አቤቱታ ማስተናገጃ ጽሕፈት ቤትን በቢሮ ደረጃ ከፍ አድርገው ቢያዋቅሩም፣ የሕዝብ ጥያቄዎች ግን በተገቢው መንገድ እየተፈቱ እንዳልሆነ ሲገለጽ ቆይቷል፡፡
በዚህ መሠረት ምክትል ከንቲባ ታከለ ይህንን ችግር ለመፍታት ለአቶ መኮንን ከፍተኛ ኃላፊነት መስጠታቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ አቶ መኮንን ቀደም ሲል የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅ ሆነው ሠርተዋል፡፡ በመቀጠልም በ40/60 ቤቶች ግንባታ ላይ የተንሰራፋውን ችግር ለመፍታት የኢንተርፕራይዙ ዋና ዳይሬክተር ሆነው ተሾመው ነበር፡፡
ከከንቲባ ጽሕፈት ቤት የወጡ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፣ አቶ መኮንን በመሬትና በመኖሪያ ቤት ላይ ባተኮሩ መሥሪያ ቤቶች የሠሩ በመሆናቸው የሕዝብን ቅሬታ ለመፍታት ያላቸው ልምድ ጠቃሚ ነው ተብለው ተሹመዋል፡፡
አቶ መኮንን ለሪፖርተር እንዳረጋገጡት ሰኞ ነሐሴ 28 ቀን 2010 ዓ.ም. የሹመት ደብዳቤ ደርሷቸዋል፡፡ ረቡዕ ነሐሴ 30 ቀን 2010 ዓ.ም. ጽሕፈት ቤቱን ተረክበው ሥራ እንደሚጀምሩም አረጋግጠዋል፡፡