Friday, December 1, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

የክቡር ሚኒስትሩ ዘመድ ከውጭ ይደውልላቸዋል

[ክቡር ሚኒስትሩ ከአንድ ዳያስፖራ ጋር እያወሩ ነው]

  • እንኳን አገርህ በሰላም ለመግባት አበቃህ፡፡
  • አመሠግናለሁ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • አገሪቱን እንዴት አገኘሃት?
  • በእውነት ክቡር ሚኒስትር አዲስ አበባ የማላውቃት ከተማ ነው የሆነችብኝ፡፡
  • ለመሆኑ ስንት ጊዜ ሆነህ ከአገር ከወጣህ?
  • ሰላሳ ዓመት እየተጠጋኝ ነው፡፡
  • ታዲያ ዕድገቱን እንዴት አየኸው?
  • ከተማዋ እኮ በፎቅ ጫካ ተውጣለች፡፡
  • ስለዚህ ዕድገት መኖሩን አረጋገጥክ ማለት ነው?
  • አይ ክቡር ሚኒስትር፣ እኔ እኮ ዕድገት የለም ብዬ ሳይሆን ስታገል የነበርኩት ዴሞክራሲያዊ መብት የለም ብዬ ነበር፡፡
  • ይኸው አገርህ እንድትገባ ያደረገህ ዴሞክራሲያዊ መብትህ አይደል እንዴ?
  • እሱን እንኳን ተውት ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ለምን ሲባል?
  • በፊት ይኼን ሥርዓት በመቃወሜ የደረሰብኝን መከራ እኔ ነኝ የማውቀው፡፡
  • ምን ተደረግኩ ልትል ነው?
  • እኔ ላይ በቀጥታ ባይደርስም፣ እዚህ የነበሩ ቤተሰቦቼ ላይ ምን ያህል መከራ ሲደርስባቸው እንደነበር መቼም አይዘነጉትም፡፡
  • አንተ እኛ ውጭ በወጣን ቁጥር ስለምታደርስብን ግፍ ይኼ ሲያንስህ ነው፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • እንደ አንተ ዓይነቱን ሰው ስናስብ እኮ ነበር የውጭ ጉዞ የሚያንገፈግፈን፡፡
  • ለምን ያስመስላሉ ክቡር ሚኒስትር?
  • የምን ማስመሰል ነው?
  • እንደዚህ ቢያንገፈግፍዎት በየወሩ ውጭ ባልወጡ ነበር፡፡
  • ውጭ የምወጣውማ ጥቅማ ጥቅሜን አስቤ እንጂ ለሌላ ለምን መስሎህ ነው?
  • እኛም እኮ እንደዚያ አምርረን የምንቃወማችሁ ለሕዝቡ ሳይሆን ለጥቅማችሁ እንደቆማችሁ ስለምናውቅ ነበር፡፡
  • አየህ መርሳት የሌለብህ ነገር እኛም እኮ የሕዝቡ አካል ነን፡፡
  • ምን ማለት ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • እኛ ስንጠቀም ሕዝቡ እንደተጠቀመ ይቆጠራል፡፡
  • በእውነት ክቡር ሚኒስትር ዘመኑ የምሕረት በመሆኑ እንጂ ለእናንተ እኮ የሚገባችሁ ጓንታናሞ ነበር፡፡
  • እኛ የሠራነው ልማት ፈጽሞ አይታይህም ማለት ነው?
  • ነገርኩዎት እኮ ከልማታችሁ ጥፋታችሁ ነው የሚብሰው፡፡
  • ለመሆኑ እዚህ ምን ልታደርግ ነው የመጣኸው?
  • አገሬ አይደል እንዴ ክቡር ሚኒስትር?
  • አይ ያው እዚያ ቢያንስ እኛን እየተሳደብክ ገንዘብ መሰብሰብ ትችል ነበር ብዬ ነው፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር እኔ እኮ ለዓመታት የታገልኩት ለገንዘብ ብዬ ሳይሆን ለሕዝቤ ተቆርቁሬ ነው፡፡
  • ስለዚህ ለሕዝብ ከተቆረቆርክ እዚህ ፓርቲ መሥርተህ ሕዝብን ትታገላለህ ማለት ነው?
  • የምን ፓርቲ ክቡር ሚኒስትር?
  • ያው ውጭም ፖለቲከኛ ስለነበርክ እዚህም በዚያው ትቀጥላለህ ብዬ ነዋ፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር እኔ እኮ ወደ አገር ቤት የተመለስኩት የጠቅላይ ሚኒስትሩን ጥሪ ተቀብዬ ነው፡፡
  • ገብቶኛል ስለዚህ አገር ውስጥ ስትገባ ፖለቲከኛ ሆነህ ነው የምትቀጥለው ወይ እያልኩህ እኮ ነው?
  • ክቡር ሚኒስትር መቼም ባለፈው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሁሉም በውጭ አገር ያለ ኢትዮጵያዊ ለአገሩ አምባሳደር ነው ሲሉ ሰምተዋል፡፡
  • ምን እያልከኝ ነው ታዲያ?
  • የአምባሳደርነትን ሥራ ዕድሜ ልኬን ስሠራው የቆየሁት ሥራ ነው፡፡
  • አሁን ግራ እያጋባኸኝ ነው፡፡
  • ከዚህ በኋላ መንግሥትን እየተቃወምኩ መኖር አልፈልግም፡፡
  • ወዴት? ወዴት?
  • ዘመኑ የመደመር በመሆኑ እኔም ተደምሬያለሁ፡፡
  • የምን ጠጋ ጠጋ ነው?
  • ክቡር ሚኒስትር መንግሥት አንድ ነገር እንዲያደርገኝ ነው የምፈልገው?
  • ምን?
  • አምባሳደር!

[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ ባለሀብት ጋ ይደውላሉ]

  • ሄሎ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • አንተ ዝም ስልህ ዝም ትላለህ እንዴ?
  • ምኑን ክቡር ሚኒስትር?
  • በፊት በዚህ ሰሞን እየደወልክ ታጨናንቀኝ አልነበር እንዴ?
  • ምን ብዬ ክቡር ሚኒስትር?
  • እንኳን አደረሰህ ለማለት ማን ቀደመኝ እያልክ ትፎካከር አልነበር እንዴ?
  • እንኳን አደረሰዎት ክቡር ሚኒስትር?
  • በቃ?
  • ምነው ክቡር ሚኒስትር?
  • ያኔ ቤቴ የከብት ማደሪያና ቄራ እስኪመስል ድረስ አልነበረ እንዴት የምታጨናንቀኝ?
  • ምን አሉኝ ክቡር ሚኒስትር?
  • በሬው አይቀርህ በጉ፣ ፍየሉ ብትል ዶሮውን አግተልትለህ አልነበር እንዴ የምታመጣልኝ?
  • መቼም በዚህኛው ዓመት በዓል ያን አይጠብቁም?
  • ለምን አልጠብቅም?
  • ሥርዓቱ እኮ ተቀይሯል፡፡
  • የምን ሥርዓት ነው የምታወራው?
  • አሁን እኮ የፍትሐዊነትና የእኩልነት ዘመን ነው፡፡
  • ቆይ! ቆይ! ቆይ! በፊት እኮ ወዳጅ ስለነበርን የምታመጣልኝ መስሎኝ?
  • እንደዚያ እንዳልሆነ መቼም ጠንቅቀው ያውቁታል፡፡
  • ታዲያ ለምን ነበር?
  • እኔ በየጊዜው ለእርስዎ ስጦታውን አዥጎደጉደዋለሁ፣ እርስዎ ደግሞ በምላሹ ለእኔ ሕንፃ አይሉ መሬት፣ ፋብሪካ አይሉ ሌላውን ያመቻቹልኛል፡፡
  • እ. . .
  • ክቡር ሚኒስትር ግንኙነታችን እኮ እከክልኝ ልከክልህ በሚለው መርህ ላይ የተመሠረተ ነበር፡፡
  • አሁን የመርህ ለውጥ አለ እያልከኝ ነው?
  • አሁንማ የፍቅር፣ የይቅርታና የመደመር ጊዜ ነው፡፡
  • እነዚህን ቃላት የማልሰማበት የት ልሂድ?
  • ክቡር ሚኒስትር ፍቅርና መደመር የሚሉት እኔ ይስማሙኛል፣ ግን ይህች የይቅርታ የምትለው ብዙም አትጥመኝም፡፡
  • እንዴት?
  • እርስዎ አሁን ያጠፉት ጥፋት በይቅርታ ብቻ የሚታለፍ አይደለም፡፡
  • ምን እያልክ ነው?
  • ስለራሴ ባወራ በዓል በመጣ ቁጥር እንዲሁ ስባንን ነበር የማሳልፈው፡፡
  • ምን ሆነህ?
  • ለእርስዎ ስጦታ የማወጣውን ወጪ እያሰብኩ ነዋ፡፡
  • ይኼን ያህል?
  • ክቡር ሚኒስትር ሥርዓቱ በመቀየሩ ነው እኮ አሁንም ከዚህ ጭንቀት የተገላገልኩት፡፡
  • ስለዚህ ስጦታ አላመጣም እያልከኝ ነው?
  • ትንሽ  ግን አያፍሩም ክቡር ሚኒስትር?
  • በምኑ ነው የማፍረው?
  • ይኸው መሪያችን በየሆስፒታሉ እየሄዱ ደም በሚሰጡበትና ቤት ለፈረሰባቸው ቤት በሚገነቡበት ዘመን፣ እርስዎ አሁንም ሊያስጨንቁን ሲሞክሩ እንዴት አያፍሩም?
  • ሰውዬ ተረጋጋ፡፡
  • ለዚያ ነው ይቅርታ ምናምን በሚሉት አላምንም የምለው፡፡
  • ምን እንዳደርግልህ ፈልገህ ነው?
  • እርስዎን ይቅርታ እንድልዎት አንድ ነገር ማድረግ አለብዎት፡፡
  • ምን?
  • ለሚቀጥሉት ሃያ ዓመታት የበዓል ወጪዬን ሊሸፍኑ ይገባዎታል፡፡
  • ማን?
  • እርስዎ!

[ክቡር ሚኒስትሩ ከደላላ ወዳጃቸው ጋር ተገናኝተው እያወሩ ነው]

  • ምነው ተከዙ ክቡር ሚኒስትር?
  • ተወኝ እባክህ፡፡
  • ምን  ተፈጠረ? አዲስ ዓመት እየመጣ መነቃቃት ነው እንጂ የምን መቆዘም ነው?
  • ግራ ገብቶኝ ነው ምን ላድርግ?
  • ክቡር ሚኒስትር የመደመር ዘመን አይደል እንዴ?
  • ጭራሽ የባሰ ደም ግፊቴን አታብስብኝ?
  • ምን ሆነዋል ክቡር ሚኒስትር?
  • ስማ እኔ ሕይወት ራሱ እየመረረኝ ነው፡፡
  • ኧረ እንደዚህ አይባልም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ይኸው የወጣትነት ዘመናችንን መስዋዕት አድርገን የተረፈን የሕዝብ ጥላቻ ነው፡፡
  • ይረጋጉ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • በየሄድንበት እኮ መሳለቂያ እየሆንን መዋረድ ነው የተረፈን፡፡
  • እንዲህማ መሆን የለበትም፡፡
  • ሻይና ቡና የምጠጣበት ቦታ እንኳን አጣሁ፡፡
  • ከጎረቤት ጋር አይጠጡም እንዴ?
  • ይህ የሚመጣ ሳይመስለኝ በልማት ሰበብ አስነስቼያቸው መቼ ጎረቤት አለኝ ብለህ ነው?
  • እሱስ እውነት ብለዋል፡፡
  • ከተማ ውስጥ ደግሞ ያኔ ቤት ተዘግቶልን እንዳልተዝናናን አሁን ግልምጫውን አልቻኩትም፡፡
  • እሱማ እኔም ሰምቻለሁ፡፡
  • በዚያ ላይ ሊያጠቁኝ ይችላሉ ብዬ ስለምሠጋ የቁም እስረኛ ሆኛለሁ፡፡
  • ለነገሩ ሰው የዘራውን ነው የሚያጭደው ሲባል ሰምቻለሁ፡፡
  • ምን እያልከኝ ነው?
  • አገሪቱ ሙሉ እስር ቤት አልነበረች እንዴ በዚህ ብቻ ካለፈልዎት ጥሩ ነው፡፡
  • ስማ ባለቤቴን ከዕድር አባረሯት፡፡
  • ዕድር ደግሞ ምን ያደርግላችኋል ብለው ነው?
  • ለማንኛውም ቢሆን ማኅበራዊ ሕይወት ያስፈልጋል፡፡
  • ለነገሩ ዕድር የሚያስፈልግዎት ዋናው ጊዜ አሁን ሊሆን ይችላል፡፡
  • እሱን እኮ ነው የምልህ፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ለእኔ ምን ጊዜም ቢሆን ባለውለታዬ ነዎት፡፡
  • ምን ያደርጋል ሕዝቡ ጠላኝ፡፡
  • እርስዎ ባይኖሩ ኖሮ እንደ እኔ ዓይነቱ ያልተማረና ብቃት የሌለው ግለሰብ ሚሊየነር መሆን ይችል ነበር?
  • እሱማ እንደ አንተ ዓይነቱን መኃይም ሚሊየነር ያደረገ ሥርዓት መገንባታችን የሚያሸልመን እንጂ የሚያስወቅሰን መሆን አልነበረበትም፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር እኔ መቼም ቢሆን ውለታዎትን አልረሳም፡፡
  • አንተ ብቻህን ምን ታደርግልኛለህ ብለህ ነው?
  • እኔማ ለዋሉልኝ ውለታ ማሸለም አለብኝ ብዬ ቆርጬ ተነስቻለሁ፡፡
  • ምንድነው የምታሸልመኝ?
  • እንዲያው ካጣሁ ገዝቼም ቢሆን አሸልምዎታለሁ፡፡
  • ምን?
  • የክቡር ዶክትሬት!

[የክቡር ሚኒስትሩ ዘመድ ከውጭ ይደውልላቸዋል]

  • ክቡር ሚኒስትር ደስ የሚል ዜና ልነግርዎት ነው፡፡
  • ምንድነው እሱ?
  • ወደ አገሬ ልገባ ነው፡፡
  • ምን አልክ?
  • ወደ አገሬ ልመለስ ነው፡፡
  • ይኼማ ፈጽሞ የማልቀበለው ነገር ነው፡፡
  • ምነው ክቡር ሚኒስትር?
  • ስማ ውጭ ያለኝን ቤት አይሉ የባንክ አካውንት የምታንቀሳቅስልኝ ሰው እንዴት ነው አገር ቤት እመለሳለሁ የምትለኝ?
  • ክቡር ሚኒስትር ከዚህ በኋላ በዚህ ሥራ አልቀጥልም፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • ዘመኑ መቼም የፍቅር፣ የይቅርታና የመደመር መሆኑን ያውቃሉ?
  • ለአንተ የሚጠቅምህ እነሱ ሳይሆኑ የእኔ ሀብት መሆኑን ረሳኸው?
  • ክቡር ሚኒስትር ከዚህ በኋላ በቃኝ፡፡
  • ውጭ አገር ሃያ ምናምን ዓመት አንደላቅቄ ካኖርኩህ በኋላ እንደዚህ ስትል አታፍርም?
  • ከዚህ በኋላ በቃኝ አልኩዎት እኮ?
  • ስማ ያ ገንዘብ በአንተ ስም መሆኑን ታውቃለህ አይደል?
  • ክቡር ሚኒስትር ገንዘቡ የእርስዎ እንዳልሆነ አያውቁም እንዴ?
  • ምን ማለት ነው? ለዘመናት የለፋሁበት ሀብት እኮ ነው?
  • ለዘመናት የዘረፍኩት ማለትዎ ነው?
  • ሰውዬ አብደሃል እንዴ?
  • ኧረ በፍፁም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • በቃ በአፋጣኝ መጥቼ ገንዘቡን ወደ እኔ ታዘዋውረዋለህ፡፡
  • እኔ ቀድሜ አዘዋውሬዋለሁ፡፡
  • ወዴት?
  • ወደ ትረስት ፈንዱ!

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

የመቃወም ነፃነት ውዝግብ በኢትዮጵያ

ስሟ እንዳይገለጽ የጠየቀችው በአዲስ አበባ ከተማ በተለምዶ የሾላ አካባቢ...

የሲሚንቶን እጥረትና ችግር ታሪክ ለማድረግ የተጀመረው አጓጊ ጥረት

በኢትዮጵያ በገበያ ውስጥ ለዓመታት ከፍተኛ ተግዳሮት በመሆን ከሚጠቀሱ ምርቶች...

የብሔር ፖለቲካው ጡዘት የእርስ በርስ ግጭት እንዳያባብስ ጥንቃቄ ይደረግ

በያሲን ባህሩ በሪፖርተር የኅዳር 9 ቀን 2016 ዓ.ም. ዕትም “እኔ...

ሀብቱንና ትርፉን እያሳደገ የቀጠለው አዋሽ ባንክ

አዋሽ ባንክ በአዲስ አበባ ከተማ አዲስ ዋና መሥሪያ ቤት...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ የሩብ ዓመት የሥራ አፈጻጸማቸውን ለተከበረው ምክር ቤት ካቀረቡ በኋላ ከምክር ቤቱ አባላት የሚነሱ ጥያቄዎችን እየተቀበሉ ማብራሪያ በመስጠት ላይ ናቸው]

ክቡር ሚኒስትር መንግሥት ለሕዝብ ይፋ ያደረገው ነገር ከምን እንደደረሰ ቢያብራሩልን? ምንድነው ይፋ ያደረገው? ጥያቄውን ትንሽ ቢያብራሩት? ከአራት ዓመት በፊት በኦጋዴን አካባቢ ነዳጅ መገኘቱን ለሕዝብ በቴሌቪዥን አብስሮ...

[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ የካቢኔና የማክሮ ኢኮኖሚ ኮሚቴ አባል የሆኑ ከፍተኛ አመራር የሚያቀርቡትን ቅሬታ እያደመጡ ነው] 

ክቡር ሚኒስትር እየሆነ ያለው ነገር በእጅጉ ስላሳሰበኝ ነው በአካል አግኝቼ ላነጋግርዎት የፈለግኩት። ጥሩ አደረግህ፣ ምን አሳሳቢ ነገር ገጥሞህ ነው? ክቡር ሚኒስትር ተወያይተንና ተግባብተን ያስቀመጥናቸው አቅጣጫዎች፣ በተለይም...

[ጉባዔው በወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮች ላይ ክቡር ሚኒስትሩን ለመጠየቅና ምላሽና ማብራሪያቸውን ለማድመጥ ተሰብስቧል። የጉባዔው አባላትም ማብራሪያ የሚሹ ጥያቄዎቻቸውን ለክቡር ሚኒስትሩ እያቀረቡ ነው]

ክቡር ሚኒስትር፣ ይህ ጉባዔ ለሚያነሳቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ለመስጠት በመካከላችን ስለተገኙ አመሰግናለሁ። ክቡር ሚኒስትር፣ ኢትዮጵያ ባለፈው ዓመት የብሪክስ አባል እንድትሆን የሰጡት በሳል አመራር የሚደነቅ ነው። አገራችን...