ሥር የሰደደ ድህነትና ሥራ አጥነት አሳሳቢ ችግሮች በመሆናቸው፣ ችግሮቹን መዋጋት ጊዜ የማይሰጠው የቤት ሥራ እንደሆነ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ አስታወቁ፡፡
ፕሬዚዳንቱ ይህን ያስታወቁት 25ኛውን ዓመት የግንቦት 20 የብር ኢዮቤልዩ በዓል አስመልክቶ ዓርብ ግንቦት 19 ቀን 2008 ዓ.ም. በብሔራዊ ቤተ መንግሥት በሰጡት መግለጫ ወቅት ነው፡፡
‹‹እየተመዘገበ ባለው የኢኮኖሚ ዕድገት ድህነትና ሥራ አጥነትን በመቀነስ ውጤታማ መሆናችን ቢረጋገጥም፣ አሁንም ወደ 22 ሚሊዮን የሚጠጋው የአገራችን ሕዝብ በፍፁም ድህነት ውስጥ የሚገኝ ነው፤›› በማለት አሁንም በርካታ ዜጎች በድህነት ውስጥ እየኖሩ እንደሆኑና እነርሱን ከድህነት ለማውጣት በጋራ መሠራት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡
ለዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠርን በተመለከተም ምንም እንኳን የተመዘገቡ አበረታች ውጤቶች ቢኖሩም አሁንም ችግሩ አለመቀረፉን አፅንኦት ሰጥተው ገልጸዋል፡፡ ‹‹ለዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠርን በተመለከተ መጠነ ሰፊ እንቅስቃሴ እየተደረገ ቢሆንም፣ ሥራ አጥነት ከከተሞች አልፎ በገጠር አካባቢዎችም ሰፊ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ችግር ከመሆን አልተላቀቅንም፤›› በማለት የችግሩን ጥልቀት በመግለጫቸው ወቅት ዳሰውታል፡፡
‹‹በመሆኑም ድህነትና ሥራ አጥነት አሳሳቢ ችግሮች መሆናቸውን በመገንዘብ፣ ሁሉን አቀፍና መዋቅራዊ ለውጥ ለማምጣት ሁላችንም በአንድ ላይ መሥራት ይጠበቅብናል፤›› በማለት ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ በመግለጫቸው ከዚህ በተጨማሪም የአገሪቱን ሰላም ማስጠበቅና መጠበቅ የሁሉም ዜጎች ኃላፊነት መሆኑን አስገንዝበው፣ ሽብርተኝነትና አክራሪነትን መዋጋት እንደሚጠበቅም ገልጸዋል፡፡
‹‹ይህ ፀረ ሕገ መንግሥት እንቅስቃሴ በየጊዜው አንገቱን ካቀረቀረበት እያገረሸ፣ ተመልሶ ደግሞ እያደፈጠ ያለና ዘላቂ መፍትሔ የሚፈልግ ጠላት ነው፤›› በማለት ሽብርተኝነትን መዋጋት የሁሉም ዜጎች ኃላፊነት እንዲሆን አስገንዝበዋል፡፡
‹‹በሃይማኖት ሽፋን የሚደረግ አክራሪነትና ተጓዳኝ ፀረ ልማት እንቅስቃሴዎችን ሁሉ ነቅተን በመከታተል ለሰላማችን ዘብ መቆም ይገባናል፤›› ሲሉ ፕሬዚዳንቱ አስታውቀዋል፡፡