Friday, March 24, 2023
- ማስታወቂያ -
- ማስታወቂያ -

ብሔራዊ ባንክ አምስት መመርያዎችን አሻሻለ

- ማስታወቂያ -

ተዛማጅ ፅሁፎች

በዶላር አካውንትና በሌተር ኦፍ ክሬዲት ላይ መጠነኛ ማሻሻያዎች ተደርገዋል

በጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) የሚመራው የማክሮ ኢኮኖሚ ኮሚቴ በቅርቡ ያፀደቃቸውን ማሻሻያዎች መነሻ በማድረግ፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ነባር መመርያዎቹን እንዳሻሻለ ታወቀ፡፡

በብሔራዊ ባንክ ገዥ ይናገር ደሴ (ዶ/ር) ተፈርመው የወጡትና ማሻሻያ የተደረገባቸው መመርያዎች አምስት ናቸው፡፡ ከእነዚህ መካከልም ዓለም አቀፍ የሐዋላ አገልግሎት፣ የውጭ ገንዘቦችና የውጭ ምንዛሪ አስተዳደርን ለማቋቋም የወጣው መመርያ፣ ትውልደ ኢትዮጵያውያንና በውጭ የሚኖሩ ዜጎች በውጭ ምንዛሪ የሚከፍቷቸውን የባንክ ተቀማጭ ሒሳቦችን የሚደነግገው መመርያ፣ ዓለም አቀፍ የክፍያ ካርዶችን የመቀበል፣ የማተምና የማስተናገድ ሥርዓትን የተመለከተው መመርያ  ይጠቀሳሉ፡፡

 በመመርያዎች ከተካተቱ ድንጋጌዎች ውስጥ ማሻሻያ የተደረገባቸው አንቀጾች ተካተውባቸው ይፋ ከተደረጉት መመርያዎች መካከል፣ ትውልደ ኢትዮጵያውያን በአገር ውስጥ ባንኮች የሚያስቀምጡት የውጭ ገንዘብ መጠን ከ50 ሺሕ ዶላር መብለጥ የለበትም የሚለው ድንጋጌ መነሳቱን የሚያመለክተው አዲሱ መመርያ ቁጥር FXD/55/2018 ከዚህ ቀደም የተቀመጠውን ገደብ ቢያነሳም፣ በውጭ ገንዘብ የሚከፈቱ ሒሳቦችንና አሠራራቸውን በተመለከተ አዳዲስና ዝርዝር ጉዳዮችን ያካተቱ አንቀጾችን አስፍሯል፡፡

በመሆኑም በውጭ ምንዛሪ የሚከፈት የባንክ ሒሳብ ዝቅተኛው ተቀማጭ ገንዘብ 100 ዶላር እንዲሆን ሲደነገግ፣ በጊዜ ገደብ የሚቀመጥ የውጭ ሒሳብ መጠን ከ5,000 ዶላር ያላነሰ እንዲሆን ተደንግጓል፡፡ ባንኮች በውጭ ገንዘቦች አማካይነት የሚከፈቱ ሒሳቦችን ለማስተዳደር በዋነኝነት መጠቀም የሚችሉት ዶላር፣ ፓውንድ ስተርሊንግ፣ እንዲሁም ዩሮ ሲሆኑ፣ እንዳስፈላጊነቱ እነዚህን መገበያያዎች በወቅቱ የምንዛሪ ተመን መሠረት እንደ ሒሳቡ ባለቤት ፍላጎት ወደ ካናዳ ዶላር፣ አውስትራሊያ ዶላር፣ ወደ ሳዑዲ ሪያል፣ ወደ ጃፓን የን፣ ወደ ድርሃም መቀየር እንደሚችሉ ተደንግጓል፡፡

 በውጭ ገንዘቦች አማካይነት ከሚከፈተው የዶላር የባንክ ሒሳብ በተጓዳኝ፣ አስመጪዎች ዕቃ ለማስመጣት በከፈቱት ሌተር ኦፍ ክሬዲት አማካይነት የጠየቁትን የውጭ ምንዛሪ ለማግኘት በሚጠባበቁበት ወቅት ዕቃ የሚገዙበትን ኩባንያ መቀየር እንደማይችሉ፣ ከዚህ ቀደም ተደንግጎ የነበረው መመርያ ተነስቶ በምትኩ የዕቃውን ዓይነት ሳይቀይሩ ዕቃውን የሚገዙበትን ኩባንያ ማንነት ግን መቀየር እንደሚችሉ በአዲሱ መመርያ ተቀምጧል፡፡ እንዲህ ያሉ ማሻሻያዎች የተደረጉባቸው መመርያዎች በአዲሱ ገዥ ፊርማ ተረጋግጠው ካለፈው ወር ጀምሮ ወደ ሥራ መግባት እንዲጀምሩ ትዕዛዝ መተላለፉን የሪፖርተር ምንጮች ገልጸዋል፡፡

በአዲሱ የብሔራዊ ባንክ አመራር መጠነኛ ማሻሻያ የተደረገባቸው አንቀጾች ቢታዩም፣ ማሻሻያዎቹ ግን በፋይናንስ ዘርፉ የሚጠበቁትን ያህል ለውጥ የተደረገባቸው ሆነው እንዳልተገኙ ምንጮች አክለዋል፡፡

spot_img
- Advertisement -spot_img

የ ጋዜጠኛው ሌሎች ፅሁፎች

- ማስታወቂያ -

በብዛት ከተነበቡ ፅሁፎች