በምድር ላይ የፈለገውን ሆኖ የተፈጠረ ሰው ማን ነው? ማንስ ነው እኔ የእንትና ብሔር ሆኜ መወለድ አለብኝ ብሎ ከማህፀን የወጣውስ ማን ይሆን? አማራ ሆኖ የተፈጠረ አለ? ኦሮሞ ሆኖ እንዲፈጠር የኦሮሞ አምላክ ያበጀውና የተፈጠረው አለ ይሆን? ትግሬ ሆኖ ለመፈጠርና ትግሬ ለመሆን ፈልጎ ወደዚህች ምድር የመጣው እሱ ማን ነው? ሶማሌው፣ ወላይታው፣ ጉራጌው፣ ጉምዙ፣ መሆን ፈልጎ እንዳልተፈጠረ እያወቅን በብሔርና በዘር ምልኪ መተብተባችን በምን ዓይነት አዚም ብንለከፍ ይሆን?
የሚቻል ቢሆንልኝና ሰው መሆኔን ብቀይር ኖሮ ምነው ሌላ ፍጡር በሆንኩና በተገላገልኩ፡፡ ከማየውና ከሚሆነው ያውም በዚህ በሠለጠነ፣ በረቀቀ ዘመን እኔ ግን ሰው መሆኔ አስጠልቶኛል፡፡ ሰው በዘሩ የሚጠቋቆምና የሚገዳደልበት ዘመን ላይ በመገኘቴ ሰው መሆኔን እረግመዋለሁ፡፡
ሰው መሆን አልፈልግም፡፡ ርግብ ወይም ሌላ ፍጥረት መሆንን አብዝቼ ተመኘሁ፡፡ ቅዠቴን በእውኔ መኖርን ናፈቅሁ፡፡ ሰው መሆን አልፈልግም፡፡ ርግብ መሆንን እመርጣለሁ፡፡ ምክንያቱም ቁራ ሆኜ ብፈጠር ሞትን አመጣብን ብላችሁ እንደ ተረገመ እንስሳ ትጠሉኝ ይሆናል፡፡ ጉጉት ሆኜም ብፈጠር ሙት ጠሪ ብላችሁ ማንጓጠጣችሁ አይቀር ይሆናል ፡፡ ሌላውንም ዓይነት የአዕዋፍ ዘር ብሆን አዝመራችንን የሚጨርስ፣ ተክሎቻችንን የሚቆረቁር ትሉኝ ይሆናል፡፡ ከወንዝ ወርጄ አምላክ የፈጠረው ውኃ ብጠጣ፣ ውኃችንን የበከለ ክፉ ፍጥረት ሳትሉኝ አትቀሩም፡፡ ስለዚህ ርግብ ሆኜ መፈጠርን እመርጣለሁ፡፡ የሰላም ምልክት እንደሆንኩ የምትዘምሩልኝ፣ ከጥላቻና ጠብ የማልመደብ ፍጥረት ብሆን ብዬ ነው ይህ ሁሉ መባተቴ፡፡
ሰው ባለመሆኔ በዘሬ የሚያንዘረዘርኝ አይኖርም፡፡ ሰው መሆኔ አልበቃ ብሎ አማራ ወይም ትግሬ፣ ጋምቤላ፣ ወላይታ፣ ሲዳማ መሆኔ ካስፈለገ ሰው መሆንን አልመኝም፡፡ ያቺን ጭሮ አዳሪ ርግብ መሆኔ ይሻለኛል፡፡ ምድር ከምትሰጠው ፍሬ ብበላ ማንም አይጮህብኝም፡፡ ሰው አይደለሁማ፡፡ ይልቁንም ሰው በስስት የሚያኖረኝ፣ የሚራራልኝ ፍጥረት ነኝና የሰላም ተሰምሳሌቱ ያደርገኛል፡፡ ለደመ ነፍሳዊቷ ፍጥረት እንዲህ የሚጨነቅ የሚጠበብ፣ ሰው የሚባል ፍጥረት ምነዋ ለራሱ ለአምሳያው አውሬ ሆነሳ እያልሁ እኔ ሰው መሆኔን ጠላሁ፡፡
ኦሮሞ፣ አማራ፣ ትግሬ፣ ጉራጌ፣ ሶማሌ፣ ሲዳማ፣ ወላይታ፣ ከንባታ፣ ጋምቤላ፣ አፋር ወዘተ . . . መሆንን ፈልጋችሁና መርጣችሁ የተፈጠራችሁ ካላችሁ እባካችሁ ንገሩኝ፡፡ እኔ ግን በእንዲህ ያለ ስሌት የሚመራውን ሰው መሆንን አልፈልግም፡፡ ለማን አቤት ልበል? ወደማንስ ልጩህ? እናት እንዴት በልጇ ትገደለለች? እንዴት በልጇ ትደፈራለች? ሕፃናት ምነዋ በሚወልዷቸው እንደ ሸምበቆ ይሰባበራሉ፣ ይገደላሉ? ምን ባጠፉ ይቀጠፋሉ፡፡ ነገ ለማንም ጥለነው ለምሔደው ከንቱና ምድራዊ ዓለም እንዴት መጤ እየተባባልን እንጠፋፋለን? ማነው ቋሚ ሆኖ የተፈጠረ? እዚች ምድር ላይ ቋሚውና ቀሪው ማን ሆኖ ነው እንዲህ ህሊና በሳተው ማንነት ታውረን የምንተላለቀው?
አሁንማ ፈራሁ፡፡ አቀንቃኞቻችን የእኛ ብሔር አባል ካልሆንክ ገነት አትገባም ብላችሁ እንዳትመጡብኝ ፈራሁ፡፡ መቼም ይህ መሆን አለበት የቀራችሁ፡፡ እንዲህ ተበክለንና ጨንቅረን በምንኖርበት በዚህ ወቅት እባካችሁ እኔ ሰው መሆን ይቅርብኝ ኦሮሞ፣ አማራ፣ ጉራጌ፣ ወላይታ፣ ሶማሌ፣ ጋምቤላ በሚሉ የብሔር ጥያቄዎች ከምወጠር ሰው አለመሆንን ተመኘሁኝ፡፡
በቡራዩ ብቻም ሳይሆን፣ በመላ አገራችን በማንነታቸው ምክንያት አምላክ ሳይጠራቸው ሰው በተባለው ፍጡር ሕይወታቸውን ላጡ ወንድሞች፣ እህቶች፣ አባቶች፣ እናቶችና ሕፃናት፣ አምላክ ነፍሳቸውን በገነት እንዲያኖርልኝ እየተመኘሁ በአካልም በመንፈስም ለተጎዱት ሁሉ ፈጣሪ ምሕረቱንና ጽናቱን እንዲሰጣቸው፣ የበቀልን ስሜት እንዲሽርላቸው ኃያሉን አምላክ እማጸናለሁ፡፡
(ከሙሉቀን ሞገስ፣ በኢሜል የተላከ)