በኢንቨስትመንትና በተለያዩ የልማት ሥራዎች ስም ተወስደው ለበርካታ ዓመታት ያለሙ የመሬት ይዞታዎችን ወደ ከተማ አስተዳደሩ የመሬት ባንክ የማስመለስ ዘመቻ ሁለተኛ ዙር በቅርቡ እንደሚጀመር፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ (ኢንጂነር) ለሪፖርተር ገለጹ፡፡
በምክትል ከንቲባነት የአዲስ አበባ ከተማን ማስተዳደር ከጀመሩ ሦስተኛ ወራቸው ላይ የሚገኙት ታከለ (ኢንጂነር)፣ በቆይታቸው ወቅት ከመሬት ጋር በተያያዘ የገጠማቸውን የተከማቸ ዝርክርክነት ‹‹ጉድ ነው›› ሲሉ ይገልጹታል፡፡
በልማት ስም ተወስደው በትንሹ አሥር ዓመትና ከዚያ በላይ ባለመልማታቸው የታጣውን ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ በቁጭት የተናገሩት ምክትል ከንቲባው፣ በመጀመርያው ዙር የመሬት ማስመለስ ተግባር ወደ አስተዳደሩ የመሬት ባንክ የተመለሰው መሬት ከ400 ሔክታር በላይ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
ይኼንን ከአሥር ዓመት በላይ ሳይለማ ታጥሮ የተቀመጠ ይዞታን መጠን ሲገልጹትም፣ ‹‹አንድ መለስተኛ ከተማ›› እንደ ማለት ነው ብለዋል፡፡
ሁለተኛው ዙር ዘመቻ በቅርቡ እንደሚጀመርም ከሪፖርተር ጋር ባደረጉት አጭር የስልክ ቆይታ አመልክተዋል፡፡
በሁለተኛው ዙር የሚካሄደው ያለሙ መሬቶችን የማስመለስ ዘመቻ በተለያዩ የልማት ዘርፎች የተወሰዱ ይዞታዎችን የሚመለከት ቢሆንም፣ በዋናነት ግን ለሪል ስቴት (የቤት ልማት) አልሚዎች ተላልፈው ለበርካታ ዓመታት ምንም ልማት ሳይካሄድባቸው ታጥረው ለተቀመጡ ይዞታዎች ምላሽ እንደሚሰጥ ተናግረዋል፡፡
‹‹በጥቂት የሪል ስቴት አልሚዎች ብቻ ከመቶ ሔክታር በላይ የመሬት ይዞታ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ሳይሰጥ ተገኝቷል፤›› ያሉት ምክትል ከንቲባው፣ ይህ ዓይነቱ ሕገወጥነት እንደሚገታና የከተማዋ ነዋሪዎችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞች በፍጥነት ለሚያረጋግጡ የልማት ሥራዎች ጥቅም ላይ እንደሚውሉ አስረድተዋል፡፡
በሪል ስቴት አልሚዎች ታጥረው ከተቀመጡ ይዞታዎች በተጨማሪ፣ በከተማ አስተዳደሩ በተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ ካባዎች (የድንጋይ ማምረቻ ይዞታዎች) ጉዳይም በሁለተኛው ዙር ዘመቻ ምላሽ እንደሚያገኝ ተናግረዋል፡፡
እሳቸው እንደሚሉት የከተማዋ ወጣቶች ሥራ አጥተው በተቀመጡበት ሁኔታና ይህ ችግርም የከተማዋ ራስ ምታት ሆኖ ሳለ፣ የድንጋይ ማምረቻ ይዞታዎችን በባለቤትነት ለበርካታ ዓመታት በብቸኝነት ይዞ ጥቅም ማጋበስ ኢፍትሐዊነት ስለሆነ ማስተካከያ እንደሚደረግበት ጠቁመዋል፡፡
‹‹የአንዳንዶቹ ካባዎች (ኳሪዎች) ባለቤቶች በውጭ የሚኖሩ ዳያስፖራዎች ናቸው፤›› ሲሉም ገልጸዋል፡፡
ምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ (ኢንጂነር) ሰሞኑን የወሰዱት ዕርምጃ በሦስት ከንቲባዎች ያልተደፈረ በአገሪቱ የፖለቲካ ማዕከል ከለላ የተሰጣቸው ይዞታዎች መሆናቸው ይታወቃል፡፡