‹‹የሰላም አስከባሪ ጓዶች በዓለም አገሮች፣ በተለይም በግጭት ውስጥ ባሉ አገሮች በመገኘት በዓለም ሰላምና አንድነት እንዲሰፍን እየሠሩ፣ የሕይወት ዋጋም እየከፈሉ ነው፡፡››
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) ዋና ፀሐፊ ባንኪ ሙን ይህን የተናገሩት፣ ተመድ ስምንት የኢትዮጵያ የሰላም ጓድ አባላትን ጨምሮ ከዓለም የተውጣጡ 129 የሰላም አስከባሪ ጓድ አባላት መስዋዕት መክፈልን ለመዘከርና ለሚመለከታቸው አካላት በቀድሞው ዋና ጸሐፊ ዳግ ሐመርሾልድ የተሰየመውን የክብር ሜዳሊያ በሰጠበት ወቅት ነው፡፡ ‹‹ኦነሪንግ አወር ሂሮስ›› (ክብር ለጀግኖቻችን) በሚል መሪ ቃል በድርጅቱ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት፣ ዓለም አቀፍ የሰላም አስከባሪ ጓዶች ቀን በተከበረበት ወቅት፣ የተሰዉ ኢትዮጵያውያን የሰላም ጓዶችን ሜዳሊያ፣ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የኢትዮጵያ ምክትል ቋሚ ተጠሪና ጉዳይ ፈጻሚ አምባሳደር ማህሌት ኃይሉ ተረክበዋል፡፡ ኢትዮጵያ ተመድ በሚመራው የሰላም አስከባሪ ኃይል መሳተፍ የጀመረችው በ1942 ዓ.ም. መጀመሪያ ነው፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ የተሳፈችበት ዘመቻም ከ1942 እስከ 1945 ዓ.ም. በኮሪያ የነበረውን ጦርነት ለማርገብ ነበር፡፡ ተመድ ከ1952 እስከ 1956 ዓ.ም. በኮንጎ ይመራው በነበረው ጦርነት ‹‹ብሎ ሄልሜት›› ዘመቻም ኢትዮጵያ መሳተፏ ይታወሳል፡፡ ከቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መንግሥት በኋላ በደርግ ዘመን (1967-1983) በአገሪቱ ውስጥ በነበረው ጦርነት ምክንያት የኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪ ኃይል በየትኛውም ዘመቻ ተሳትፎ አያውቅም፡፡ ከሁለት አሠርታት በኋላ ግን የሰላም አስከባሪ ጓድ ውስጥ በተለያዩ የአፍሪካ አገሮች መሳተፍን ቀጥሎበታል፡፡ ፎቶው የተመድ ዋና ጸሐፊ ባንኪ ሙን በሰላም አስከባሪ ጓድ ውስጥ ሆነው መስዋዕትነት ለከፈሉት ኃይሎች መታሰቢያ በጠቅላይ ጽሕፈት ቤቱ የአበባ ጉንጉን ሲያስቀምጡ ያሳያል፡፡