‹‹በቀደምት አባቶች ተጀምሮ ዘመናትን ያስቆጠረው ወርቃማ የአስተዳደር፣ የግጭት አፈታትና የማኅበራዊ ተግባቦት ባህል በሰነድ መልክ ለማስተላለፍ እንዲቻል ‹ኮቱ – ዱፌ› በመጽሐፍ መልክ ተዘጋጅቶ እንዲቀርብ ከምክንያቶቹ አንዱ የሆነው የመልካም አስተዳደርና ዴሞክራሲ ባህል በአገር ደረጃ እንዲዳብር እገዛ ለማድረግ ነው፡፡››
ይህ መሰንበቻውን የኅትመት ብርሃን ያየው የኮሎላ ደ. ‹‹ኮቱ – ዱፌ›› የተሰኘው መጽሐፍ በመግቢያው ላይ የሠፈረው ኃይለ ቃል ነው፡፡ በኦሮሞ አገር በቀል ዕውቀት ላይ የሚያጠነጥነው መጽሐፉ በመግቢያው እንደተጠቀሰው፣ በኦሮሞ አባቶች መማክርት የስብሰባ ሥርዓት የ‹‹ኮቱ – ዱፌ›› የአማርኛ ትርጉም ከሌላው የዘልማድ የፍትሕ አሰጣጥ ሥርዓት ጋር ተመሳሳይ ቢመስልም ከቃል ትርጉም ጀምሮ በጣም ይለያል፡፡
ቃሉ በቁሙ በጥሬ ትርጉሙ ሲመለከቱት ‹‹በላ – ልበልሃ›› ከሚለው ባህላዊ የፍትሕ አሰጣጥ ሥርዓት ጋር ይመሳሰላል፡፡ ይሁን እንጂ በሚያቅፈው ጉዳይ ወሰን ክልልም ሆነ በጥልቁ እንዲሁም በማኅበረሰባዊ ፍትሕና ሰብአዊ ፋይዳው ላይ ጠለቅ ብሎ የሚሄድ ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች በተለይም ልሂቃን አባቶች/አባገዳዎች በሚሰበሰቡበት ወቅት ኮቱ – ዱፌ የሚለውን አጠራር /ኮቱ/ ኑ እንመካከር በሚል ትርጉም አዘውትረው ሲጠቀሙበት እናያለን፡፡ ኮቱ የሚለው በአፋን ኦሮሞ ቀጥተኛ የቃል ትርጉም ና እንደ ማለት ሲሆን፣ ዱፌ የሚለው ደግሞ መጣሁ እንደማለት ነው፡፡ ይሁንም እንጂ በዚህ መጽሐፉ አገባብ በቀረበበት ሁኔታ ግን ኮቱ – ዱፌ ማለት ‹‹ስማ-ሰማሁ›› የሚለውን የመጠራራት በሐሳብ የመቀራረብ፣ የመጠያየቅ፣ የመወያየትና የመመካከር ጥልቅ የመግባባት ትርጉም ይይዛል፡፡
ኮቱ ዱፌ በስድስት ክፍሎች የተከፈለ ሲሆን እነሱም የአገር በቀል ዕውቀት ሥርዓት ማብራሪያዎች፣ የአባ ገዳ ሥርዓት መዋቅርና አሠራር ማሳያ፣ የገዳ ሥርዓትና ሕግጋት፣ የኮቱ ዱፌ (ስማ-ሰማሁ) ተሳትፎ መስፈርቶች፣ በምርመራ ለመታየት የሚበቁ የኮቱ ዱፌ ሥርዓት የግጭት ደረጃዎች ናቸው፡፡ አባሪዎችና ተጨማሪ መረጃዎች በመጨረሻው ክፍል ተካትተዋል፡፡ የመጽሐፉ ዋጋ 91 ብር ነው፡፡