ከተመሠረተ ከሁለት ዓመት ተኩል በላይ የሆነው የኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙኃን ምክር ቤት በሕጋዊ መንገድ ሊመዘገብ ባለመቻሉ፣ ክልከላው ተነስቶለት በአስቸኳይ እንዲመዘገብ ጠየቀ፡፡
የመገናኛ ብዙኃን ምክር ቤቱ ጥር 3 ቀን 2008 ዓ.ም. ከፍተኛ የመንግሥት ተጠሪዎች በተገኙበት በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አዳራሽ የምክር ቤቱን ሕገ ደንብና የሥነ ምግባር ደንብ ፈርመው በተቀበሉ 19 መሥራች አባላት ቢቋቋምም፣ የበጎ አድራጎ ድርጅቶችና ማኅበራት ኤጀንሲ እንዲመዘግበው ያቀረበው ጥያቄ እስካሁን ተቀባይነት አላገኘም፡፡ በዚህ ምክንያት ምክር ቤቱ በሚዲያ ኢንዱስትሪ ውስጥ ማበርከት የሚችለውን አስተዋጽኦ ማበርከት እንዳልቻለ፣ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው ባወጣው መግለጫ ገልጿል፡፡
‹‹የሚዲያ ምክር ቤቱ አይመዘገብም ተብሎ የተሰጠው ምክንያት በእኛ በኩል ሕገ መንግሥታዊ መተማመኛ የተሰጠውን የአንቀጽ 29 እና የአንቀጽ 31 መብታችንንና ነፃነታችንን ሳንለቅና ሳናስረክብ የምንቀበለውና የምናሻሽለው ሆኖ አላገኘነውም፤›› ያለው የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ መግለጫ፣ የማኅበራት ማደራጃ አዋጅ በርካታ ችግሮች ያሉበት መሆኑ በመንግሥት ታውቆ እንደገና እንዲታይ ከተደረጉት ሕጎች መካከል መሆኑን ጠቁሟል፡፡ ሆኖም ሕጉ አሁን ባለበት ሁኔታ የሚዲያ ምክር ቤት ጥያቄ ማስተናገድ ይችላል ብሎ እንደሚያምን ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው በመግለጫው አስታውቋል፡፡
‹‹መንግሥትና ኅብረተሰቡ እምነታችንን፣ ዓላማችንንና ጥያቄያችንን እንዲረዱልን እየጠየቅን ኤጀንሲው የምዝገባ ማመልከቻችንን እንደገና እንዲመለከትልን፤›› ሲል ጥያቄውን አቅርቧል፡፡ መንግሥት የፕሬስ ነፃነትና ሐሳብን የመግለጽ ነፃነትን የሚያደናቅፉ አንዳንድ አዋጆች ለማሻሻል ፈቃደኛ ሆኖ የተግባር እንቅስቃሴ ጀምሯል ያለው የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው፣ የመገናኛ ብዙኃንና መረጃ ነፃነት ሕግ፣ የፀረ ሽብር ሕጉና የብሮድካስት አዋጅ መሻሻል አለባቸው ብሏል፡፡
ስለሆነም ሕጎቹን በማሻሻል እንቅስቀሴ ውስጥ ሙያዊ የሐሳብ ግብዓቶችን ለማበርከት ዝግጁ መሆኑንና የተግባር እንቅስቃሴ መጀመሩን በመግለጽ፣ ‹‹መንግሥት አዋጆቹን በማሻሻል ሒደት ውስጥ የመገናኛ ብዙኃን ምክር ቤትን ዕውቅና ሰጥቶ እንዲሳተፍ እንጠይቃለን፤›› በማለት ጥያቄውን አቅርቧል፡፡
ምንም እንኳን የመገናኛ ብዙኃን ምክር ቤቱ የሕጋዊ ሰውነት ጥያቄው ምላሽ ባያገኝም፣ የአገሪቱ ሚዲያ የሚንቀሳቀስበትን የሕግ ማዕቀፍ የሚጨምር፣ ነፃነቱንና ኢንዱስትሪውን ለሚያጉላሉ ጥያቄዎች መልስ የሚያፈላልግ፣ ለሕጎቹና በአጠቃላይ ለሥርዓቱ መሻሻል አስተዋጽኦ ማድረግ የሚያስችል ሥራ መጀመሩን አስታውቋል፡፡ በዚህ ሒደት ውስጥ ባለፉት ሁለት ዓመታት ምክር ቤቱ ሳይመዘገብ አንዳንድ እንቅስቃሴዎችን ሲያደርግ መቆየቱን ገልጿል፡፡ ከዋቢ አሳታሚዎች ማኅበር ጋር በመተባበር ባለፈው ሩብ ምዕተ ዓመት በአገሪቱ ሐሳብን የመግለጽ ነፃነትና የመገናኛ ብዙኃን ዘርፍ ዕድገት ላይ የላቀ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ሁለት ሰዎች፣ የመታሰቢያ ሽልማት ማዘጋጀቱን እንደ አብነት ጠቅሷል፡፡
በሚዲያ ተቋማትና የጋዜጠኞች ማኅበራት አማካይነት የተቋቋመው የመገናኛ ብዙኃን ምክር ቤት በአሁኑ ወቅት የአባላቱ ቁጥር 29 ደርሰዋል፡፡