‹‹አሊ በርኪ ጐታ ኦሮሞ›› [አሊ በርኪ የኦሮሞ ጀግና] የተሰኘው መጽሐፍ በ1969 እና 1970 ዓ.ም. በኢትዮጵያና በሶማሊያ መካከል በተደረገው ጦርነት ወቅት ከፍተኛ ተጋድሎ የፈጸሙትን አሊ በርኪን የሕይወት ታሪክ የሚዳስስ ነው፡፡ ከአሊ የልጅነት ሕይወት ተነስቶ ስለጦርነቱ በዝርዝር ያወሳል፡፡ አሊ በጦርነቱ ወቅት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከቱ ቢሆንም ታሪካቸው ሰፋ ባለመንገድ በጽሑፍ አልቀረበም፡፡
የጀግንነት ታሪክ የያዘው መጽሐፉ በኦሮምኛ ቋንቋ የተጻፈ ሲሆን፣ ግንቦት 21 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሞ ባህል ማዕከል ተመርቋል፡፡ ደራሲው ኢሳያስ ሆርዶፋ ለሪፖርተር እንደገለጸው፣ የላቀ የጦር ሜዳ ጀብዱ ተሸላሚ የሆኑት ሰው ታሪክ እንዳይረሳ በጽሑፍ ለማስቀመጥ ሲል መጽሐፉን ጽፏል፡፡ ‹‹በ1969 ዓ.ም. የሶማሊያ ሠራዊት ሐረርጌ ክፍለ ሀገርን በያዘበት ወቅት፣ ከምዕራብ ወለጋ ቤጊ ከተማ ተመልምለው የዘመቱና ከፍተኛ ጀብዱ የፈጸሙ የሚሊሺያ ሠራዊት አባል ታሪክ ነው፡፡ ለአገራችን ዳር ድንበር መከበር አስተዋጽኦ ያደረጉ ናቸው፤›› ሲል ገልጿል፡፡
እንደ ደራሲው ገለጻ፣ በተለያየ ቋንቋ የሚጽፉ ደራስያን የተለያየ ብሔረሰብ ተወላጅ የሆኑ ጀግኖች የአገሪቱን ዳር ድንበር በመጠበቅ ረገድ ያበረከቱትን አስተዋጽኦ በጽሑፎቻቸው ማሳየት አለባቸው፡፡ ‹‹በአገሪቱ ነፃነት የሁሉም ብሔረሰብ ጀግኖች አሻራ ስላለበት አስተዋጽኦዋቸው መታየት አለበት፤›› ሲል ይገልጻል፡፡
መጽሐፉ አሊ በትውልድ ቀዬያቸው ውስጥ በአደን ታዋቂ ከነበሩበት ጊዜ አንስቶ ሕይወታቸውን ይዳስሳል፡፡ ለነፃነት ያደረጉትን ተጋድሎም ያትታል፡፡ ይህም ለትውልዱ መማሪያ እንደሚሆን የታሪኩ ባለቤት ይናገራሉ፡፡ ‹‹ታሪኩ የኔ ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ ታሪክ ነው፡፡ ወራሪዎች አገር ጥሰው በገቡበት ወቅት እምቢ ለአገሬ እምቢ ለነፃነቴ ብለን ለኢትዮጵያ አንድነት የወደቅነውን ሰዎች ታሪክ መጽሐፉ ያሳያል፤›› ሲሉ አሊ ስለመጽሐፉ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
መጽሐፉ ትውልዱ ለነፃነት የሚቆምና አገሩን የሚጠብቅ እንዲሆን እንደሚያነሳሳ ያምናሉ፡፡ በጦርነቱ ወቅት ከጀግንንታቸው የተነሳ ‹‹አሊ በርኬ ገልገለ ዱፉ ደንቀራ በልበለን ጩፉ›› አሊ በርኬ ማታ ይመጣልና ቶሎ በራችሁን ዝጉ ይባል እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ ዘጠኝ ጊዜ በጥይት ተመተው ሁለት ጊዜ በሳንጃ ቢወጉም እሳቸውና ሌሎችም ጀግኖች በቆራጥነት መዋጋታቸው አገሪቱን እንዳቆየ ይገልጻሉ፡፡ ታሪካቸው በመነገሩም ደስተኛ ናቸው፡፡ ‹‹መከፋፈል ቀርቶ በአንድነት ይህችን አገር መጠበቅን ለትውልዱ አደራ እላለሁ፤›› ይላሉ፡፡
ደራሲው ከዚህ ቀደም ‹‹ሀዊ››፣ ‹‹የሮን ሲፈዲስቱ››፣ ‹‹ዮሚ ላታ››፣ ‹‹ጽጌረዳና ሌሎችም አጫጭር ልቦለዶች›› የተሰኙ መጻሕፍት ያሳተመ ሲሆን፣ መጽሐፉ በ40 ብር እየተሸጠ ነው፡፡