ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ወደ ሥልጣን ከመጡ ወዲህ ለመጀመርያ ጊዜ በሚያደርጉት የአውሮፓ ጉበኝት ከ20 እስከ 25 ሺሕ የሚጠጉ በአውሮፓ ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ጋር በጀርመን ፍራንክፈርት እንደሚገናኙና ንግግር እንደሚያደርጉ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በየ15 ቀኑ በሚሰጠው መግለጫው አስታወቀ፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ይህን ያስታወቀው ሐሙስ ጥቅምት 8 ቀን 2011 ዓ.ም. በቃል አቀባዩ መለስ ዓለም አማካይነት፣ በጉብኝቱና ባለፉት 15 ቀናት በተከናወኑ ዲፕሎማሲያዊ ሥራዎች ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት ነው፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደ አውሮፓ የሚያቀኑት ወደ ፈረንሣይና ጀርመን ሲሆን፣ ጉብኝቱም የፈረንሣይ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮንና የጀርመኗ መራሒተ መንግሥት አንገላ መርከል ባደረጉላቸው ግብዣ መሠረት መሆኑን ቃል አቀባዩ አስረድተዋል፡፡
ለአንድ ሳምንት ያህል በሚዘልቀው ጉብኝት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሁለቱ መሪዎች ጋር በሁለትዮሽ፣ በቀጣናዊና እንዲሁም በዓለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ እንደሚመክሩ ቃል አቀባዩ አክለው አስረድተዋል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ በጀርመን ፍራንክፈርት ከተማ ‹‹አንድ ሆነን እንነሳ ነገን እንገንባ›› በሚል መሪ ቃል፣ በመላው አውሮፓ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በተገኙበት ንግግር እንደሚያደርጉም ይጠበቃል፡፡
ፍራንክፈርት አዘጋጅ እንድትሆን የተመረጠችበትን ምክንያት ያብራሩት ቃል አቀባዩ፣ ‹‹የጠቅላይ ሚኒስትሩ የአውሮፓ ጉዞ የመጨረሻ ጉዞ ጀርመን በመሆኑና በአንፃራዊነትም በርካታ ቁጥሮች ያላቸው ኢትዮጵያውያን ስለሚኖሩ፣ እንዲሁም ለብዙዎቹ ኤምባሲዎቻችን አማካይ ቦታ ላይ ስለሚገኝ ነው፤› ብለዋል፡፡
ከተለያዩ የአውሮፓ አገሮች የሚወከሉ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በአገሪቱ መጪው ዕድል፣ የመንግሥት ዕቅድና ክንውንና አሁን በተጀመረው የለውጥ እንቅስቃሴ ውስጥ በሚኖራቸው አስተዋጽኦ ላይ ጥያቄያቸውን፣ ፍላጎታቸውንና ራዕያቸውን እንደሚያቀርቡና ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ሐሳብ የሚለዋወጡበት ዕድል እንደሚፈጥርም ተገልጿል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ ሥልጣን የያዙ ሰሞን ወጪ ለመቀነስ በማሰብ፣ ሚኒስትሮች የውጭ አገር ጉዟቸውን እንዲቀንሱ ወይም እንዲሰርዙ መመርያ መስጠታቸው ይታወሳል፡፡ የእሳቸው ጉብኝት ከዚህ መርህ አንፃር እንዴት ይታያል? ተብሎ ከሪፖርተር ለቀረበላቸው ጥያቄ ቃል አቀባዩ፣ ‹‹ወጪ መታሰብ አለበት፡፡ የታክስ ከፋይ ኅብረተሰብ ሀብት አላስፈላጊ በሆነ መንገድ መውጣት የለበትም፡፡ ይህ ማለት ግን ከሌሎች አገሮች ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት አታደርግም ወይም ትመንናለህ ማለት አይደለም፤›› ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
‹‹የተመረጡ ሥራዎች ይሠራሉ፡፡ በተለይም የውጭ ግንኙነት ዘርፍ ባህሪው ሆኖ እየተጓጓዝክ የምትሠራው ሥራ ነው፡፡ ሌሎች የሚመጡትን ያህል ስትጋበዝም መሄድ ያስፈልጋል፡፡ ከዚያ ጋር የሚጣረስ ነገር የለውም፡፡ ውስን ሀብታችን ግን በጥንቃቄ መጠቀም አለብን፡፡ ይኼ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርም ቋሚ መርህ ነው፤›› በማለት አብራርተዋል፡፡