ሰኔ 3 ቀን 2008 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 22ተኛ ሳምንት ፕሮግራም ኢትዮጵያ ቡና ከአዋሳ ከተማ እያደረገ በነበረበት ወቅት በ30ኛ ደቂቃ ላይ የተቆጠረውን ጎል ከኦፍ ሳይድ አቋቋም ውጪ ነው በማለት በተቃወሙት ደጋፊዎች ምክንያት ውድድሩ ተቋረጠ፡፡
ከጎሎ መቆጠር በኋላ ወደ ሜዳ በመግባት ከዳኛው ጋር እሰጥ አገባ ውስጥ የገቡት ተመልካቾቹ በፀጥታ ኃይሎች አማካይነት እንዲወጡ መደረጉን ምንጮች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ ውድድሩ እንደገና እንዲጀመር ቢያደርግም ከስምንት ደቂቃ በላይ ማስኬድ አልተቻለም፡፡ ከተመልካች የሚወረወረው የመጠጫ ፕላስቲክ ውድድሩን ሙሉ በሙሉ ለማቋረጥ ምክንያት ሆኗል፡፡
የአዋሳ ከተማው አስቻለው ግርማ ባስቆጠረው ግብ ምክንያት የጀመረው ግብግብ ከስታዲየም ውጪ ቀጥሎ በደጋፊዎች ላይ ጉዳት መድረሱ ተጠቁሟል፡፡ ጉዳት የደረሰባቸው ደጋፊዎችም በአንቡላንስ ተወስደዋል፡፡ ከጊዜ ወደ ጊዜ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ከእግር ኳስ እንቅስቃሴ ይልቅ የሁከትና የብጥብጥ መናኸሪያ መሆኑ እየቀጠለ ነው፡፡ ግንቦት 14 ቀን 2008 ዓ.ም. ጎንደር ላይ በዳሽን ቢራና በኢትዮጵያ ቡና ደጋፊዎች መካከል ተፈጥሮ በነበረው ብጥብጥ የብዙ ተመልካቾችን አካል ያጎደለ መሆኑ ይታወሳል፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን በሁለቱ ክለቦች መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት ተከትሎ የቅጣት ውሳኔ ቢያሳልፍም ጉዳዩ ሥር እየሰደደ መምጣቱን ቀጥሏል፡፡
ቀደም ብሎ በክልል ከተሞች እንደዚህ ዓይነት ችግር ሲስተዋል የነበረ ቢሆንም አሁን ደግሞ አዲስ አበባ ስታዲየም ላይ እንዲህ ዓይነት ሁከቶች መከሰታቸው ችግሩን ይበልጥ ያባብሰዋል የሚለው ብዙዎችን ያስማማ ጉዳይ ነው፡፡ ምንም እንኳን ወደ ስታዲየም የሚያመራው ተመልካች ጨዋታ ለማየት ቢመጣም በዳኝነት ላይ በሚኖረው ቅሬታ በሚፈጠረው አታካሮ ከፀጥታ ኃይሎች ጋር በሚደረግ ግብግብ ንብረትና የአካል ጉዳት እየደረሰ ይገኛል፡፡
ለዚህም የሚመለከተው አካልና የክለብ አመራሮች መፍትሔ ሊያበጁለት እንደሚገባ የስፖርቱ ቤተሰብ ዘወትር ይጠይቃል፡፡