ጥቅምት 11 ቀን 2011 ዓ.ም. በትግራይ ክልል ራያ ዞን አላማጣ ከተማ በማንነት ጥያቄ ሠልፍ ከወጡ ሰዎች መካከል የሦስት ሰዎች ሕይወት ማለፉ ተገለጸ፡፡ የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ጉዳዩን በሚመለከት ባወጣው መግለጫ ሞት የተከሰተው ከፀጥታ ኃይሎች ጋር በተፈጠረ አለመግባበት መሆኑን፣ በፀጥታ አካላት ላይም ጉዳት መድረሱን አክሏል፡፡
የክልሉ መንግሥት ባወጣው መግለጫ፣ ‹‹የሕዝብን የማንነት ጥያቄ በማስመሰል ሌላ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት እየተደረገ ያለው ሩጫ በማንኛውም መመዘኛ ተቀባይነት የሌለው ተግባር ነው። ይህ ሳያንስ የዜጎችን ሰላም፣ ፀጥታና ደኅንነት ለመጠበቅ ከተሰማራው የፀጥታ መዋቅር ጋር መጋጨትና በማነሳሳት ዕርምጃ እንዲወስድ መግፋት ደግሞ በፍፁም መደገም የሌለበት ተግባር ነው፤›› ሲል ሁኔታውን ገልጾታል፡፡
ክልሉ በመግለጫው አክሎም፣ ‹‹ማንኛውም ጥያቄ ያለው አካል ሕጋዊና ሰላማዊ በሆነ መንገድ ጥያቄውን ማቅረብና መልስ ማግኘት በሚቻልበት ክልል ውስጥ ፍላጎትን በኃይል ለማስፈጸም መንቀሳቀስ ተቀባይነት የሌለው ድርጊት ሲሆን፣ የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ እጁን ያስገባ ማንኛውንም አካል በቸልታ እንደማያልፈው በዚህ አጋጣሚ ይገልጻል፤›› ብሏል፡፡
የክልሉ መንግሥት ይኼንን ይበል እንጂ፣ አንዳንድ ሪፖርቶች የሟቾች ቁጥር ሰባት እንደሚደርስ ይጠቁማሉ፡፡ ከትግራይ ክልል አላማጣ የተፈናቀሉና በወሎ ቆቦ አካባቢ የተጠለሉ ተፈናቃዮች ከአማራ ብዙኃን መገናኛ ኤጀንሲ ጋር ባደረጉት ቆይታ፣ ‹‹በአፍ መፍቻ ቋንቋችን እንማር፣ እኛ የወሎ አማራ ነን ባልን በትግራይ ክልል ልዩ ፖሊስ ግፍና መከራ ደርሶብናል፤›› ሲሉ የተናገሩ ሲሆን፣ በአካባቢው ከተጠለሉ ተፈናቃዮች ጋር ውይይትም ተካሂዷል፡፡
በጉዳዩ ላይ መግለጫ ያወጣው የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት በበኩሉ፣ ‹‹ሰሞኑን ወልቃይት አካባቢ በማንነታችን ብቻ ጥቃት ደረሰብን ያሉ የወልቃይት አማራዎች ተፈናቅለው በጐንደር ከተማ የሰፈሩ ሲሆን፣ በሌላ በኩል በራያ አላማጣ በተፈጠረው ግጭት በሰው ሕይወትም ጭምር ጉዳት አድርሷል፤›› ብሏል፡፡ የትግራይ ክልል ችግሩን ለመግታት በሚያደርገው ጥረት ለማገዝ ዝግጁ መሆኑንም የክልሉ መንግሥት አስታውቋል፡፡
በግጭቱ ከሞቱት በተጨማሪ ቀላልና ከባድ የአካል ጉዳት የደረሰባቸው መኖራቸውን፣ የሕክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው እንደሆነም ታውቋል፡፡