በቅዱስ ላሊበላ አራት ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ላይ የተደቀነውን አደጋ ለመከላከል የአማራ ክልል መስተዳደር ምክር ቤት 30 ሚሊዮን ብር መመደቡን የክልሉ ባህል ቱሪዝም ቢሮ አስታወቀ፡፡
ለቅርሱ ሥጋት የሆኑትና ከአሥር ዓመት በላይ በቤተክርስቲያናቱ የተተከሉትን የብረት መጠለያ ምሰሶዎችን ለማንሳት 300 ሚሊዮን ብር እንደሚስፈልግ መነገሩን ተከትሎ ነው የገንዘብ ማሰባሰቡ የተጀመረው፡፡ ለቅርሱ ዘላቂ ጥገና የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን ለበጀት ዓመቱ 20 ሚሊዮን ብር መመደቡ ይታወሳል፡፡
የክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ልዑል ዮሐንስ በሰጡት መግለጫ የላሊበላ ዓለም አቀፍ ቅርስ ከተደቀነበት የመፍረስ አደጋ ለመታደግ ሥራዎች ተጀምረዋል ብለዋል።
የቅርሱን ጥገና ለመጀመር ቀደም ሲል የጉዳት መጠን ልየታና እንዴት ሊጠገን ይችላል የሚል የጥናት ሰነድ በባለሙያዎች መዘጋጀቱንና ለጥገናውም 300 ሚሊዮን ብር እንደሚያስፈልግም መታወቁን ሳይገልጹ አላለፉም፡፡
በመንግሥቱ ድርጅት የባህል ተቋም ዩኔስኮና የአውሮፓ ኅብረት ድጋፍ በ2000 ዓ.ም. የተሠሩት መጠለያዎች ለአምስት ዓመታት ብቻ እንዲቆዩ ቢታሰብም ለተጨማሪ ስድስት ዓመታት መቆየታቸውና መጠለያዎቹን የደገፉት የብረት ምሰሶዎች መሬቱን እየሰነጣጠቁ በመሆኑ እንዲነሱ በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር በየካቲት 2010 ዓ.ም. መወሰኑ ይታወሳል፡፡
በወቅቱ እንደተገለጸው፣ በላሊበላ በአሳሳቢ ሁኔታ ውስጥ ካሉት ቅርሶች መካከል እነ ቤተ መድኃኔዓለም፣ ቤተ መርቆሪዎስ በዕድሜ ብዛት በደረሰባቸው ተፈጥሯዊ ጫና ምክንያት እየተፈረካከሱ ፈተና ውስጥ መግባታቸውን ቅርሱን ለመጠገን የተወሰዱ ዕርምጃዎች አንፃራዊ ለውጥ ከማምጣት ይልቅ ወደተባባሰ ችግር እያመሩ መሆኑንም ተመልክቷል፡፡
የቅርስ ጥገና በርካታ መዋለ ንዋይ በመጠየቁ ከመንግሥት በተጨማሪ ሌሎችም እንዲሳተፉበት እንደሚደረግ፣ በቀጣይም አደጋ ላይ ያሉ የላሊበላ አብያተ ክርስቲያናትን በሙሉ ለመጠገን የሚያስችል የፋይናንስ አቅም ለመፍጠር የሚሠራ አገራዊ ኮሚቴ እንደሚቋቋምም የባህል ቱሪዝም ሚኒስቴር ማሳወቁ ይታወቃል።
ባለፈው መስከረም መገባደጃ ‹‹ታሪክና ቅርስ እየፈረሰ አዲስ ታሪክ አይሠራም፣ ቅርሳችን ሲፈርስ እያየን ዝም አንልም፣ ላሊበላን መታደግ ኢትዮጵያን መታደግ ነው. . .›› እነዚህንና መሰል ኃይለ ቃሎችን በሰሌዳ ይዘው በላሊበላ ከተማ ሠልፍ መውጣታቸው ይታወሳል፡፡
በተያያዘ ዜናም ባለፈው ሳምንት የተካሄደው ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ 37ኛ ዓመታዊ ስብሰባውን ሲያጠናቀቅ ባወጣው የአቋም መግለጫ በላሊበላ አብያተ ክርስቲያናት ጉዳይ፣ ቅዱስ ሲኖዶሱ ከመንግሥት ጋራ እንዲመክር ማሳሰቡ ታውቋል፡፡