የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ባለሟሎች በ1927 ዓ.ም.
(ፎቶ ከድረ ገጽ)
*****
መንግሥት ሲጋብዝ
መቶ ሺሕ ብር ይውጣ
ሰው ጠግቦ እንዲጠጣ
ውስኪው ብዙ ብዙ፤
ቢራም ብዙ ብዙ
ምግብም ብዙ ብዙ፤
ሁሉም በገፍ ይምጣ፤
ሰው ጠግቦ እንዲወጣ፤
እየበላህ ብላ
እየጠጣህ ጠጣ፤
ከሕዝብ ነው እንጂ
ካንተ ኪስ አይወጣ፤
ስትፈልግ ደፍተህ ሌላ አዲስ አስሞላ፤
ምግብም ተትረፍርፏል– ተፍተህ ደግመህ ብላ፤
ምን ይጨመርልህ ምን ነገር –ጎደለ?
ለሒሳቡ አታስብ– ከፋይ ገበሬ አለ፡፡
- ሞገስ ሀብቱ
******
‹‹ዱለት ሆነሃል አትለኝም?››
ከብዙ ጊዜ የመጠጥ ሱስ በኋላ ሰውየው በጤና መታወክ ወደ ሐኪም ቤት ይሄዳል፡፡ ጠቅላላ ምርመራ ከተደረገለት በኋላ ሐኪሙ ስማ ሰውየ በመጠጥ የተነሳ ያመመህ ጨጓራ፣ ጉበት፣ ኩላሊትና ሐሞት ነው ቢለው፣ በሽተኛውም መልሶ ምን ይኼን ሁሉ ያዘረዝርሃል ባጭሩ ዱለት ሆነሃል አትለኝም ብሎ አለው፡፡
******
ሼክ ናስረዲንና ስስታሙ ሰው
በአንድ ወቅት በጣም ስስታም ነገር ግን በጣም ሀብታም የሆነ የናስረዲን ጎረቤት ነበር፡፡ ናስረዲን ግን በጣም ድሃ ነበር፡፡ ናስረዲንም አላህ 1000 ፓውንድ እንዲሰጠው ይፀልይ ነበር፡፡ ታዲያ አንድ ቀን ስስታሙ ሰው የናስረዲንን ፀሎት ሲሰማ የመስጊዱ ጣሪያ ላይ ወጥቶ 999 ፓውንድ ሊወረውርለት አሰበ፡፡ ወደ መስጊዱም በመሄድ ናስረዲን አምላኩ ገንዘብ እንዲሰጠው ሲፀልይ ስስታሙ ሰው ገንዘቡን ማዝነብ ጀመረ፡፡ ናስረዲንም በጣም ተደስቶ ገንዘቡን ከሰበሰበ በኋላ መቁጠር ጀመረ፡፡ በመጨረሻም 1 ፓውንድ መጉደሉን ሲያውቅ፣ ወደ ሰማይ አንጋጦ “አምላክ ሆይ፣ 1 ፓውንድ አጉድለህብኛልና ዕዳ አለብህ፡፡” አለ፡፡
በሚቀጥለው ቀን ጎረቤቱ ወደ ናስረዲን ቤት ሄዶ “አዳምጥ፣ ፀሎትህን ሁሉ ሰምቻለሁ በፀሎትህም የለመንከውን ገንዘብ 1000 ፓውንድ ካነሰ አልቀበልም ማለትህን ሰምቻለሁ፡፡ እኔ ግን 999 ፓውንድ ስሰጥህ ተቀብለሃል” አለው፡፡ ናስረዲንም “ስለምን እያወራህ እንደሆነ አላውቅም፡፡ ውጣ ከቤቴ” አለው፡፡
ስስታሙም ሰው ወደ ዳኛ ወሰደው፡፡ መንገድ ከመጀመራቸው በፊት ግን ስስታሙ ሰው በቅሎውን ጭኖ ኮቱን ለበሰ፡፡
ይህንን ባየ ጊዜ ናስረዲን “እኔ በጣም አርጅቻለሁ፣ በእግሬ መጓዝ አልችልም፡፡ በጣም ስለበረደኝም ወደ ዳኛ እንድሄድ ከፈለክ ኮትህን ለብሼ በቅሎህን መሳፈር አለብኝ፡፡” አለው፡፡
ስስታሙም ሰው 1000 ፓውንዱን ማጣት ስላልፈለገ በሃሳቡ ተስማማ፡፡ ከዚያም ጉዟቸውን ወደ ፍርድ ቤት ቀጠሉ፡፡ ናስረዲንም ዳኛውን በርቀት ባየው ጊዜ ኮት ለብሶ በቅሎዋን የተሳፈረው እሱ መሆኑን ዳኛው እንዲያይለት መጮህ ጀመረ፡፡ በዚህ ጊዜ ቃዲው ድምፁን ሰምቶ ሲመለከት ሽማግሌውን ሰው ከበቅሎው ላይ አየው፡፡ ናስረዲን ከበቅሎዋ ላይ ወርዶ ካሰራት በኋላ ከሳሽና ተከሳሽ ከዳኛው ፊት ቀረቡ፡፡
ከሳሹ ስስታም ሰው “ጌታዬ ይኼ ሽማግሌ አምላክን ‘1000 ፓውንድ ስጠኝ፡፡ ከዚያ ያነሰም ሆነ የበለጠ አልቀበልም’ ብሎ ሲፀልይ ሰምቼ ልፈትነው በማሰብ 999 ፓውንድ ብሰጠው ቃሉን አጥፎ ገንዘቡን ወስዷል፡፡” ብሎ ከሰሰው፡፡
ናስረዲንም በተራው “ጌታዬ ይህ ሰው እብድ ነው፡፡ ይኼንን ማረጋገጥ እችላለሁ፡፡ በእርስዎ ፊት ይኼንን የለበስኩትን ኮት የእኔ ነው ይላል፡፡” አለ፡፡
ስስታሙም ሰው አቋርጦት “በእርግጥ ኮቱ የኔ ነው!” ብሎ ጮኸ፡፡ ናስረዲንም በመቀጠል “በኮቱ ብቻ አይደለም የማረጋግጠው፡፡ በበቅሎ ስመጣ እርስዎ ጌታዬ አይተዋል፡፡ እሱ ግን በቅሎው የኔ ነው ይላል፡፡” አለ፡፡
ስስታሙም ሰው በድጋሚ “በእርግጥም የእኔ ነው::” ብሎ ጮኸ፡፡ ቃዲውም እውነትም ስስታሙ ሰው እብድ ነው ብሎ በማሰብ አባረረው፡፡ ወደ የቤታቸው ሲመለሱ ስስታሙ ሰው እጅግ በጣም አዝኖ ነበር፡፡
ናስረዲንም ጠርቶት “በሰውና በአምላክ መሃከል ለምን ለመግባት ትሞክራለህ? ሁለተኛ ይኼ ድርጊት እንዳይለምድህ፡፡” ብሎ ገንዘቡን መለሰለት፡፡
- በሃጂ አብዱሰታር መሃመድ በሽር የተተረከ የሐረሪ ተረት
*****
ሚስት የተቀያየሩ ባሎች
ሚስትዎት ከጓደኛዎ ጋር ፍቅር መጀመሯን ቢያውቁ በቤትዎ ሰላም ሳይሆን ፀብ ሊፈጥሩ ይችላሉ፡፡ በኡጋንዳ ያሉት ጓደኛሞች ግን ጉዳዩን ወደ ፀብ ከመቀየር ይልቅ ሚስቶቻቸውን ለመቀያየር ተስማምተዋል፡፡
ኦልአፍሪካ እንደዘገበው፣ ሁለቱ የቅርብ ጓደኛሞች ሚስቶቻቸውን ለመቀያየር የተስማሙት፣ ሁለቱም ሚስቶቻቸውን መሰራረቃቸውን ካመኑ በኋላ ነው፡፡
በዕለተ ሰንበትም ሕዝብ በተሰበሰበበት፣ ስቴቨን ወሶንጋ እና ዴቪድ ዎሲ የሚስት መቀያየር ሥነሥርዓት ፈጽመዋል፡፡
ሚስተር ወሶንጋ የሚስተር ዎሲ ባለቤት የነበረችውን ሚስ ሳራ ሙዱዋ ሲወስድ፣ በተቃራኒው ሚስተር ዎሲ የሚስተር ወሶንጋ ባለቤት የነበረችውን ሚስ አኔት ናማታካን ወስዷል፡፡
በኡጋንዳ ቡካሲ አስተዳደር የመቀያየር ሥነሥርዓቱን ያስፈጸሙት ካውንስለር ሚስ ሮዝ ማናያናያ፣ ‹‹ባልና ሚስቶቹ የደረሱበት ውሳኔ ትክክል ነው፡፡ አስመስሎ ከመኖር ልባቸው የፈቀደውን መፈጸማቸው መልካም ውሳኔ ነው፤›› ብለዋል፡፡