ከዘመነ አክሱም ቀጥሎ በአሥረኛው ምእት ከመጣው የዛጉዌ ሥርወ መንግሥት የሚመዘዝ ሐረግ አላቸው፡፡ ሰሎሞናዊው ሥርወ መንግሥት በ13ኛው ምእት ሥልጣኑን ሲቆናጠጥና ነገደ ዛጉዌ በዋግሹም ሥር ሲተዳደር 20ኛው ምእት ዓመት ላይ የነበሩት አባታቸው ዋግሹም ወሰን ኃይሉ (የአርበኛው ሌተና ጄኔራል ኃይሉ ከበደ ልጅ) በሰቆጣ መንበሩ ላይ ስለነበሩ በልጅነታቸው የምስለኔነት ማዕረግ ይዘው ነበር፡፡ ልጅ ተፈሪ ወሰን ኃይሉ፡፡
ገጸ ታሪካቸው እንደሚያመለክተው፣ የዋግሹም ምስለኔ እንደመሆናቸው መጠን በልጅነታቸው ዳኝነት መቀመጥ ባለሥልጣን መሻርና መሾም የአደባባይ ተግባር አከናውነዋል፡፡
በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመን (1923 – 1967) ትምህርታቸውን በ1940ዎቹና 50ዎቹ በአዲስ አበባና በእንግሊዝ የተከታተሉት ልጅ ተፈሪ በ1954 ዓ.ም. ወደ አዲስ አበባ ከተመለሱ በኋላ በማስታወቂያ ሚኒስቴር በጋዜጠኝነት በተለይ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ክፍልና በሕዝብ ግንኙነት ሥራ ላይ ተሰማርተው ነበር፡፡ በጋዜጠኝነታቸው የአድማጮች ምርጫ (Listener’s Choice) መሰናዶዋቸው ጉልህ ድምፃቸው በአድማጮች ታዋቂ እንደነበር ዘመነኞቹ ያስታውሳሉ፡፡ እንዲሁም ‹‹ፓሬድ›› (PARADE) የሚባል ፕሮግራም አቅራቢና ቀጥሎም የእንግሊዝኛው ቋንቋ አገልግሎት ተጠባባቂ ኃላፊ ሆነውም ሠርተዋል፡፡
በ1960ዎቹ አጋማሽ በኢትዮጵያ ውስጥ የተከሰተውና ለንጉሡ መውረድ ሰበብ የነበረው ረሃብን በሚመለከት፣ በ1966 ዓ.ም. በቢቢሲ ጋዜጠኛ ጆናታን ዲምቢልቢ በወጣው ‹‹የተደበቀው ረሃብ›› (The Unknown Famine) ፊልም ቁልፍ ሚና መጫወታቸው ይነገራል፡፡
ልጅ ተፈሪ በዘመነ ደርግ ከ1967 ዓ.ም. ጀምሮ ለአምስት ዓመታት የማስታወቂያ ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ፣ ከ1971 እስከ 1976 ዓ.ም. በባህል ሚኒስቴር ሥር በነበረው ፊት የፊልም ማዕከል፣ በኋላ የኢትዮጵያ ፊልም ኮርፖሬሽን የፊልም ፕሮዳክሽን ኃላፊ ነበሩ፡፡ በወቅቱ ለአምስተኛው የአብዮት በዓል የተዘጋጀው የአብዮቱን የአምስት ዓመታት ጉዞ የሚያሳየው ድል ፊልም ካዘጋጁት መካከል ይገኙበታል፡፡ በ1960ዎቹና 80ዎቹ በተዘጋጁትና በዓለም አቀፍ መድረክ ላይ ከቀረቡት ፊልሞች ‹‹ሻፍት ኢን አፍሪካ››፣ ‹‹ዘ ቢግ ባታሊዮን›› እና በኃይሌ ገብረሥላሴ ሕይወት ላይ የተመሠረተው ‹‹ኢንዱራንስ›› (ጽናት) የሳቸው አሻራ አርፎበታል፡፡
ልጅ ተፈሪ፣ ፊልም ኮርፖሬሽንን ከለቀቁ በኋላ ያመሩት ወደ ቀድሞው የዕርዳታ ማስተባበሪያና ማቋቋሚያ ኮሚሽን (ዕማማኮ) ሲሆን፣ ለሰባት ዓመታት ያህል በሕዝብ ግንኙነት ኃላፊነት የሠሩበት አጋጣሚ በ1977 ዓ.ም. የተከሰተው አስከፊውን ረሃብ የተከሰተበት ነበር፡፡ የወቅቱ ረሃብ በሚመለከት በአገር ውስጥና በዓለም አቀፍ ደረጃ ይካሄድ የነበረውን የሚዲያ ሽፋን ሥምሪታቸው ነበር፡፡
ከመንግሥታዊ ሥራቸው በ1982 ዓ.ም. ከተሰናበቱ በኋላ ለሦስት ዓመታት በአሜሪካ ኤምባሲ በዩናይትድ ስቴትስ ኢንፎርሜሽን ሰርቪስ የኢንፎርሜሽን ኃላፊነት በኋላ የራሳቸውን የሚዲያ የምክር አገልግሎት ድርጅት ዋግ ኮሙዩኒኬሽን ኢንተርፕራይዝ በማቋቋም በግልና በመንግሥት በአማርኛ የሚታተሙበትን ጋዜጦች ዜናና የአስተያየት ጽሑፎች ወደ እንግሊዝኛ ተርጉሞ ኢንፎርሜሽን ዳጀስት (Information Digest) የተባለ የዕለትና ሰቨን ዴይስ አፕዴትስ (Seven Days Update) የተሰኘውን ሳምንታዊ የዜና ሕትመቶች በማውጣትና በማሰራጨት፣ በአዲስ አበባ የሚኖሩ የዓለም አቀፍ ድርጅቶችና የኤምባሲ ሠራተኞች ስለኢትዮጵያ ትክክለኛውን ግንዛቤ እንዲያገኙ በማድረግ ድርጅቱ ትልቅ አገልግሎት ሲሰጥ ኖሯል፡፡
በልዩ ልዩ ምሁራዊ ጉባኤዎች በመካፈልና የራሳቸውን ጥናታዊ አስተዋጽኦ በማቅረብ የሚታወቁት ልጅ ተፈሪ ወሰን፣ እንደ አንጋፋው ጋዜጠኛና መምህር ማዕረጉ በዛብህ አገላለጽ፣ አዳዲስ ጠቃሚ ሐሳቦችን በማመንጨት፣ ሐሳቦችን ወደ ዕቅዶችና ወደ ተግባሮች በማሸጋገርና በመምራት ልዩ ስጦታና ዕውቀት የነበራቸው ሰውን በግል፣ በማኅበርም ሆነ ባገር ደረጃ ለመርዳት ወደኋላ የማይሉ ሰው ነበሩ፡፡
ልጅ ተፈሪ ወሰን በ1957 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የእንግሊዝኛ ዜና አቅራቢ የነበሩትን ወ/ሮ ታቦቱ ወልደሚካኤልን በማግባት አንድ ወንድና አንዲት ሴት ልጅን አፍርተዋል፡፡ አንዲት የልጅ ልጅንም አይተዋል፡፡
በቀድሞው ወሎ ጠቅላይ ግዛት ዋግ አውራጃ ዋና ከተማ በሆነችው በሰቆጣ ግንቦት 1 ቀን 1932 ዓ.ም. ከአባታቸው ከዋግሹም ወሰን ኃይሉና ከእናታቸው ከወ/ሮ ጀምበርወርቅ ብሩ የተወለዱት ልጅ ተፈሪ ወሰን፣ ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በአሜሪካ ያረፉት ሰኔ 3 ቀን 2008 ዓ.ም. ሲሆን ሥርዓተ ቀብራቸው አባታቸው በተቀበሩበት መንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሰኔ 11 ቀን 2008 ዓ.ም. ተፈጽሟል፡፡