ላለፉት ሰባት ወራት የተካሄደውን የለውጥ ጅምር እንደሚያደንቅ የገለጸው ሰማያዊ ፓርቲ፣ ይህ መልካም የለውጥ ጅማሮ መሠረት የሚይዘው ግን በተቋም ደረጃ ሲገነባ ነው አለ፡፡ አሁንም የተቋማት ግንባታ ቅድሚያ እንዲሰጠው አሳሰበ፡፡
ፓርቲው ይህን ጥያቄ ያቀረበው ረቡዕ ኅዳር 5 ቀን 2011 ዓ.ም. የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ወቅት ነው፡፡
‹‹መንግሥት የዴሞክራሲ ተቋማት ግንባታንና የአዋጅ ማሻሻያዎችን ለማድረግ እየሄደበት ያለው ዘገምተኛ አካሄድ ያሳስበኛል፤›› በማለት ፓርቲው የገለጸ ሲሆን፣ ‹‹በአሁኑ ጊዜ ምንም ዓይነት በሚባል ደረጃ የአዋጅ ማሻሻያም ሆነ ተቋማት እንደገና የማዋቀር ሒደት እየተከናወነባቸው መሆኑን የሚገልጽ አሳታፊ እንቅስቃሴ ሰማያዊ ፓርቲም ሆነ የኢትዮጵያ ሕዝብ እየተመለከተ አይገኝም፤›› በማለት፣ ለጉዳዩ አጽንኦት ተሰጥቶት እንዲሠራ ጥያቄ አቅርቧል፡፡
‹‹ባለፉት 27 ዓመታት ለይስሙላ ምርጫ አድርጌያለሁ በማለት ሥልጣን ላይ የቆየው የገዥው መንግሥት ተገን ከሆነው የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ጋር በተያያዘ፣ ያሉ አዋጆችም ሆኑ ተቋሙን እንደገና ሁሉም ባለድርሻዎች በተገኙበት የማዋቀር ሥራ ለማከናወን ጥቂት ሙከራ እንኳን አለመኖሩ ሥጋታችንን በትልቁ ያንረዋል፤›› በማለት፣ የተቋሟት ግንባታ ጉዳይ ዋነኛ አጀንዳ አለመሆኑ የሥጋቱ ምንጭ እንደሆነበት አስታውቋል፡፡
ከኤርትራ ጋር የተጀመረው የሰላም ግንኙነት በሕግና ተቋማዊ በሆነ መንገድ መከናወን እንደሚኖርበት ፓርቲው አስገንዝቧል፡፡ በመሆኑም መንግሥት በማናቸውም ሁኔታ ከኤርትራ መንግሥት ጋር የሚያደርገው ግንኙነት በፍፁም ‹‹የሆይ ሆይታ›› መሆን እንደሌለበት አሳስቧል፡፡
‹‹አሁን ላይ የሚገኘው መንግሥት እንደ ከዚህ ቀደም ዓይነት ስህተቶች እንዳይሠራና መርህ አልባ ግንኙነት እንዳይደገም መታረም ያለባቸው ጉዳዮችንም በሕግና ተቋማዊ በሆነ መንገድ እንዲፈጽም፣ ይህንንም በተመለከተ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ማናቸውንም ነገር ግልጽ መሆን አለበት፤›› በማለት ሰማያዊ ፓርቲው ጠይቋል፡፡
በቅርቡ በሰብዓዊ መብቶች ጥሰትና በሙስና ወንጀል የተጠረጠሩ ግለሰቦች ለሕግ መቅረባቸውንና በጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ የተጀመረውን ዕርምጃ እንደሚደግፍ አስታውቆ፣ ‹‹ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ የአገርና የሕዝብ ሀብት ሲዘርፉና ሲመዘብሩ የነበሩ ሌቦች ለሕግ የማቅረብ ጅማሮውን አጠናክሮ ይቀጥልበት፤›› በማለት ድጋፉን ገልጿል፡፡