‹‹ፋይናንስ ለአገራዊና ለወጪ ንግድ ዕድገት፣›› በሚል ርዕስ በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን አዳራሽ ባለፈው ሳምንት በተካሄደው ኮንፈረንስ ወቅት የወጪ ንግዱን የተመለከተ ጽሑፍ መወያያ ከነበሩ ጉዳዮች አንዱ ነበር፡፡
በብሔራዊ ፕላን ኮሚሽን፣ የኢኮኖሚ አገልግሎቶች ፕላን ዳይሬክቶሬት አማካይነት ተዘጋጅቶ የኢትዮጵያ የወጪ ንግድ አፈጻጸምን በማስመልከት የቀረበው የዳሰሳ ጥናት እንደሚጠቁመው፣ የአገሪቱ የወጪ ንግድ በተለያዩ ችግሮች የታጠረ ስለመሆኑ አጽንኦት የሚሰጥ ነበር፡፡ በወጪና ገቢ ንግድ መካከል ያለው ልዩነት እየባሰበት እንደመጣ ያመለክታል፡፡ የ20 ዓመታት የአገሪቱን የወጪ ንግድ አፈጻጸም በአማካይ በማስላት ትንታኔ በተሰጠበት በዚህ ጽሑፍ መሠረት፣ ከ1992 እስከ 2010 ዓ.ም. ባሉት ዓመታት ውስጥ የተመዘገበውን የወጪ ንግድ አፈጻጸም አሳይቷል፡፡ በ2010 ዓ.ም. የተመዘገው የወጪ ንግድ መጠን 184.28 ቢሊዮን ብር ነበር፡፡ ይሁንና ለገቢ ንግድ የዋለው ገንዘብ በአማካይ የ21.84 በመቶ ዕድገት በማሳየት የ502.11 ቢሊዮን ብር መጠን ነበረው፡፡
በዚህም የተነሳ የአገሪቱ የንግገድ ሚዛን ጉድለት ከላይ በተጠቀሱት ዓመታት በአማካይ በ24.33 በመቶ ሲሆን፣ የወጪ ንግድ ከአጠቃላይ የአገር ውስጥ ምርት ያለው ድርሻ 12.12 በመቶ ሆኖ ይህም ድርሻ በአማካይ በዜሮ በታች ወደ 1.3 በመቶ አሽቆልቁሏል፡፡
በ2ዐ17 ዓ.ም. ኢትዮጵያ በዝቅተኛው እርከን የመካከለኛ ገቢ ካላቸው አገሮች ተርታ (በዓመት ከ1000 ዶላር በላይ ገቢ ያላቸው ዜጎች) እንድትመደብ የሚያስችሉ ሥራዎች እየተሠሩ እንደሚገኙ ተጠቅሷል፡፡ ተደጋግሞ እንደሚነገረው፣ ላለፉት አሥር ዓመታት ኢኮኖሚው ፈጣን ዕድገት ስለማስመዝገቡ ቢሆንም፣ የብሔራዊ ፕላን ኮሚሽን ጽሑፍ ግን ፈጣኑን ዕድገት ያስገኙ የልማት ሥራዎች የሚያስፈልጋቸውን የውጭ ምንዛሪ ማግኘት እንዳልቻሉ ይጠቁማል፡፡
ለዳሰሳ ጥናቱ ከ1989 እስከ 2010 ዓ.ም. ያሉ ጊዜ አጠቃላይ የገቢና ወጪ ንግድ አፈጻጸም መረጃዎችን፣ የውጭ ምንዛሪ ተመንን፣ ጠቅላላ የአገር ውስጥ ምርትን እንዲሁም የዋና ዋና ላኪዎችን ሐሳብ ለመቃኘት ተሞክሯል፡፡ የጥናቱ ዓላማ ለወጪ ንግዱ ዝቅተኛ አፈጻጸም በምክንያትነት ሊነሱ የሚችሉ ነጥቦችን በመተንተን ወደፊት የተሻለ አፈጻጸም ማስመዝገብ የሚቻልበትን የፖሊሲ ምክረ ሐሳብ ማቅረብ ነበር፡፡
የወጪ ንግድ ምርቶችና የመዳረሻ አገሮችን በተመለከተ ጥናቱ እንደሚጠቅሰው፣ ከ1989 ዓ.ም. እስከ 2010 ዓ.ም. ባሉት ዓመታት ውስጥ ለወጪ ገበያ ሲቀርቡ የነበሩ ምርቶች በአማካይ የ17.6 በመቶ ዕድገት በማሳየት የ24.34 ቢሊዮን ብር አማካይ ገቢ ማስገኘታቸው ተመልክቷል፡፡ ይሁን እንጂ በነዚሁ ዓመታት ለወጪ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን በዓይነት፣ በብዛትና በጥራት እሴት ጨምሮ የማቅረብ ብቃት ችግሮች እንደነበሩም ተጠቅሷል፡፡ በ1989 ዓ.ም. የኢትዮጵያ የወጪ ንግድ መዳረሻ የነበሩት 72 አገሮች፣ በ2010 ዓ.ም. ወደ 144 ጨምረዋል፡፡ ቁጥራቸው በአማካይ በአራት በመቶ ከፍ ብሏል፡፡
በ2010 ዓ.ም. ከአሥር ዋና ዋና የአገሪቱ የወጪ ንግድ መዳረሻ አገሮች ውስጥ አራቱ የአፍሪካ ናቸው፡፡ ጂቡቲ የ13.5 በመቶ፣ ጋና የ8.7 በመቶ፣ ሳዑዲ ዓረቢያ የ6.8 በመቶ፣ ሱዳን የ6.8 በመቶ፣ አሜሪካ የ5.7 በመቶ፣ እንግሊዝ የ3.5 በመቶ ሶማሊያ የ3.2 በመቶ፣ አውስትራሊያ የ2.6 በመቶ፣ የመን የ2.4 በመቶ፣ ቻይና የ2.1 በመቶ አማካይ ድርሻ አላቸው፡፡ እነዚህ አሥር አገሮች ከጠቅላላው የአገሪቱ የወጪ ንግድ መዳረሻ አገሮች ውስጥ 50 በመቶው ሦስት ይይዛል፡፡ ከአንዳንድ አገሮች ጋር ያለው ግንኙነት ክፍያ ነው፡፡ ለምሳሌም ከቻይና በ1989 ዓ.ም. ቻይና ከአገራችን የሸቀጦች ወጪ ንግድ ያላት ድርሻ 0.07 በመቶ የነበረ ሲሆን፣ ይኸው ድርሻ በ2010 ዓ.ም. ወደ 9.68 በመቶ ከፍ ሊል ችሏል፡፡
ከ1989 እስከ 2010 ዓ.ም. ለወጪ ገበያ ሲቀርቡ ከነበሩ ልዩ ልዩ የወጪ ምርቶች የተገኘው ገቢ ዕድገት ከማሳየት ባሻገር መጠነኛ የወጪ ንግድ መዳረሻ አገሮች በስብጥር የጨመሩበት ጊዜም ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ዕድገቱ ኢትጵዮጵያ ለወጪ ገበያ የምታቀርበውን ምርት ስብጥርና ብዛት ማሻሻል ያልቻለችበት ጊዜንም የሚወክል ነው፡፡
‹‹በጥቂት የወጪ ምርቶችና ዘርፎች ላይ ተወስነን መቆየታችን በዓለም አቀፍ ንግድ የመሳተፍ አቅማችን ውስን እንዲሆን፣ ሥራዎችንና የመፍጠር አቅማችን እንዲገታ እንዲሁም ለተፈጥሮ አደጋዎችና ለዓለም አቀፍዊ የኢኮኖሚ መዋዠቅና ያለንን ተጋላጭነት ከፍ አድርጎታል፤›› ተብሎ ተገልጿል፡፡ የዳሰሳ ጥናቱ የፖሊሲ ምክረ ሐሳቦችን ያቀረበ ሲሆን፣ ከእነዚህም ውስጥ የወጪ ንግድ ምርቶችን በመጠንና በዓይነት አብዝቶ በማምረት፣ በጥራት ለዓለም ገበያ አቅርቦ በተወሰኑ ምርቶች ላይ ብቻ ተገድቦ በመቆየት ሊከሰት የሚችለውን የተጋላጭነት አደጋ መቀነስ የሚቻልበትን አካሄድ ይጠቁማል፡፡ የወጪ ንግድን ከማበረታታቱ ጎን ለጎን፣ የገቢ ምርቶችንም የመተካት ሥራዎችን በስፋት መሥራት ወሳኝ መሆኑን አመላክቷል፡፡
በሌላ በኩል፣ የዓለም አቀፍ ገበያ መዳረሻዎቻችንን በማስፋት ለአገሪቱ የወጪ ንግድ ምርቶች የተሻለና አስተማማኝ የገበያ አማራጮችን ማግኘት አንዱ መፍትሔ ነው፡፡ የቀላል ማኑፋክቸሪንግ ምርቶች ላይ እሴቶችን በመጨመርና የተሻሻሉ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ከዓለም አቀፉ የምርት እሴት ሰንሰለት ተሳታፊ መሆንና የተሻሻሉ ዝርያዎችንና ልዩ ልዩ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የግብርናውን ዘርፍ ምርትና ምርታማነት ማሳደግ ወሳኝ መሆናቸውን አመላክቷል፡፡
የአኅጉራዊና ዓለም አቀፋዊ የንግድ ስምምነቶችንና ግንኙነቶችን ማጠናከር ትኩረት ሊደረግበት እንደሚገባ የጠቀሰው የፖሊሲ ምክረ ሐሳቡ፣ የአገልግሎት ወጪ ንግድን በማስፋፋት በቀጥታ ከሚገኘው የውጭ ምንዛሪ ግኝት ባሻገር በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆን ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ከዚህም ሌላ ዘርፉ ከፍተኛ የሆነ የመነሻ ካፒታል፣ በርካታ የሰው ኃይልና የኢንቨስትመንት ፋይናንስ የማይጠይቅ በመሆኑ በርካታ አነስተኛ ድርጅቶች እንዲሳተፉበት ሁኔታዎችን ማመቻቸት ያስፈልጋል፡፡ ይህንንም አጋጣሚ በመጠቀም ሌሎች አዳዲስ ሥራዎችን መጀመር የሚቻልበትን ሁኔታዎች ማመቻቸት ለወጪ ንግዱ ዕድገት ጠቃሚ ይሆናል ተብሏል፡፡
ከዚህ ጋር በተያያዘ ውጫዊና ውስጣዊ ሁነቶችን በተመለከተ ደግሞ፣ በወጪ ንግድ ዘርፍ የተሰማሩ አካላትን አፈጻጸም የሚወስኑ ውጫዊ ሁነቶችን በየጊዜው በመከታተል ተገቢውን ማስተካከያ ማድረግና በወጪ ንግድ ዘርፍ የሚሠሩ የፈጠራና የምርምር ሥራዎችን ማበረታታት ወሳኝ ጉዳይ መሆኑን ለማመላከት ሞክሯል፡፡
ጥናት አቅራቢው አቶ ውብሸት ካሳ እንደገለጹት፣ የወጪ ንግድ ገበያዎች ላይ መደበኛ ጉብኝቶችና በዓለም ገበያ ዙሪያ በሚካሄዱ ጥናቶች ላይ ተሳታፊ በመሆን የኩባንያዎች ሠራተኞችን በቂ የዓለም አቀፋዊ የንግድ ሥራ ዕውቀት እንዲኖራቸው ማስቻል ከተጠቀሱት ሐሳቦች ውስጥ ነው፡፡ የወጪ ገበያ ላይ ያተኮረ የማቀነባበርና የመገጣጠም፣ የመለዋወጫ ዕቃዎችን የማምረት፣ የውል ውል (ሰብ–ኮንትራት) ስምምነቶች፣ ብራንድ ምርቶችን በአገር ውስጥ የማምረት እንዲሁም የራስ ብራንድ የሆነ ምርት ማምረቶችን መከተል ጊዜ ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ አለመሆኑም ተጠቁሟል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ፣ ተገቢውን ቅድመ ሁኔታ በማሟላት የኤሌክትሮኒክ ድንበር ተሻጋሪ ግብይት ማስጀመርና በዓለም አቀፉ ንግድ ከታችኛው የእሴት ሰንሰለት ወደ ላይኛው የእሴት ሰንሰለት መሸጋገር የሚያስችል ስትራቴጂ በመንደፍ ሊተገበር እንደሚገባ አመላክቷል፡፡ በመሆኑም የአገራችንን የወጪ ምርት ፕሮሰስድና ማኑፋክቸርድ ወደሆኑ ከፍተኛ እሴት የታከለባቸው ምርቶች የማስፋፋቱ ጉዳይ አሁንም በወጪ ንግዱ ዘርፍ የተጋረጠ ችግር እንደሆነ የቀጠለ ስለመሆኑም ጥናቱ አስታውሷል፡፡