ከመንግሥታዊ ኃላፊነታቸው በመልቀቃቸው ምክንያት ከሕዝብና ቤቶች ቆጠራ ኮሚሽን ውክልናቸውን ባጡ አባላት ምትክ፣ 20 አዳዲስ አባላት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማክሰኞ ኅዳር 18 ቀን 2011 ዓ.ም. ቃለ መሃላ ፈጸሙ።
በ2010 ዓ.ም. ይካሄዳል ተብሎ ይጠበቅ የነበረውን የሕዝብና ቤቶች ቆጠራ በበላይነት ለሚመራው የሕዝብና ቤቶች ቆጠራ ኮሚሽን፣ ኮሚሽነርና ሌሎች አባላት በ2009 ዓ.ም. በምክር ቤቱ ተሾመው ነበር።
የኮሚሽኑ አመራርና አባል እንዲሆኑ የሚሰየሙት ከኃላፊነቱ ጋር ተዛማጅ ከሆኑ የፌዴራል መንግሥት መሥሪያ ቤቶች ሚኒስትሮችና የክልል መንግሥታት ርዕሰ መስተዳድሮች ናቸው።
በዚህም መሠረት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኰንን ኮሚሽነር ሆነው በወቅቱ ሲሾሙ፣ ሌሎች 21 አባላት ደግሞ ከፌዴራል መንግሥት ተቋማትና ከክልል መንግሥታት ርዕሰ መስተዳድሮች ተሾመው ነበር።
ይሁን እንጂ ከኮሚሽነሩ አቶ ደመቀና ከአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር በስተቀር፣ የተቀሩት የኮሚሽኑ አባላት በአሁኑ ወቅት በኃላፊነት ላይ አይደሉም። በመሆኑም በአሁኑ ወቅት በሥልጣን ላይ የሚገኙ ተተኪ አመራሮች የኮሚሽኑ አባል ሆነው ቃለ መሃላ እንዲፈጽሙ በኮሚሽነሩ አቶ ደመቀ መኰንን የቀረበለትን ጥያቄ፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤቶ ተቀብሎ ቃለ መሃላ እንዲፈጽሙ አድርጓል፡፡
በዚህም መሠረት ተተኪ የኮሚሽኑ አባል በመሆን ቃለ መሃላ የፈጸሙት የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪሃት ካሚል፣ የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሺዴ፣ የግብርና ሚኒስትሩ አቶ ኡመር ሀሰን፣ የትራንስፖርት ሚኒስትሯ ወ/ሮ ዳግማዊት ሞገስ፣ የጤና ጥበቃ ሚኒስትሩ አሚር አማን (ዶ/ር)፣ የፕላንና ልማት ኮሚሽነር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር)፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሚኒስትር አቶ ሽመልስ አብዲሳ፣ የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስትር አቶ ጃንጥራር ዓባይ፣ የሴቶች ወጣቶችና ሕፃናት ጉዳይ ሚኒስትር ወ/ሮ ያለም ፀጋይ፣ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል የጥናትና ፐብሊኬሽን ዘርፍ አስተባባሪ አቶ ተመስገን ቡርቃ፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ወ/ሮ ኬሪያ ኢብራሂም ከፌዴራል ተቋማት የተወከሉ ናቸው።
የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብርሃም ተከስተ (ዶ/ር)፣ የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ምክትል ርዕሰ መስተዳድር የሆኑት አቶ ላቀ አያሌው፣ የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ወ/ሮ ጠይባ ሁሴን፣ የሶማሌ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አደም ፋራህ፣ የሐረሪ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ፣ የደቡብ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኤልያስ ሽኩር፣ የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ አብደላ አህመድ ሙሐመድ፣ የቤንሻንጉል ጉሙዝ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አበራ ባዬታና የጋምቤላ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ታንካይ ጆክን የክልል መንግሥታትን በመወከል የኮሚሽኑ አባላት ሆነው ቃለ መሃላ ፈጽመዋል።
አቶ ደመቀ መኰንን በኮሚሽነርነት የመምራትና አባላቱን የመሰብሰብ ኃላፊነታቸውን ሲቀጥሉ፣ የአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ርዕሰ መስተዳድርም በአባልነት ቀጥለዋል።