በማያቋርጡ ግዙፍ ግንባታዎች ውስጥ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል፣ ያለውን ቋሚ ንብረትና የሀብት ምጣኔውን ለማወቅ የሚያስችል ጥናት እንዲያካሂድለት ከፌር ፋክስ አፍሪካ ፈንድ ኩባንያ ጋር ስምምነት ተፈራረመ፡፡
ሐሙስ ኅዳር 20 ቀን 2011 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈጻሚ አብርሃም በላይ (ዶ/ር) እና የፌር ፋክስ አፍሪካ ፈንድ ኩባንያ ሊቀመንበር አቶ ዘመዴነህ ንጋቱ ተፈራርመዋል፡፡
በፊርማ ሥነ ሥርዓቱ ላይ እንደተገለጸው፣ የሀብት ቆጠራና ግምቱ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ወደፊት ከአገር ውስጥ ወይም ከውጭ የፋይናንስ ምንጮች ራሱን ችሎ ለመበደር በሚፈለግበት ጊዜ የተሟላ መረጃ እንዲኖረው ያደርጋል፡፡
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ያሉትን ንብረቶችና የሀብት መጠኑን አይታወቅም፡፡ ንብረቶቹ ያልተመዘገቡ በመሆናቸው ነው ዋጋቸው አይታወቅም የተባለው፡፡
በስምምነቱ መሠረት ጥናቱ ሲጠናቀቅ ተቋሙ ያለውና የሌለው ሀብት ተለይቶ የሚመዘገብ ሲሆን፣ የሀብት መጠኑም ምን ያህል ዋጋ እንዳለው ተለይቶ ይታወቃል ተብሏል፡፡
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈጻሚ አብርሃም (ዶ/ር) እንዳሉት፣ የሚካሄደው ጥናት ለዓለም አቀፍ የፋይናንስ ሪፖርት አዘገጃጀትና አቀራረብ ጠቀሜታ ይኖረዋል፡፡
‹‹ስምምነቱ ውጤታማ እንዲሆን ተቋሙ ክትትል ያደርጋል፡፡ ከዚህ በኋላም በሰው ኃይል አቅም ግንባታ ላይ ትኩረት ተደርጎ ይሠራል፤›› ሲሉ ዋና ሥራ አስፈጻሚው (ዶ/ር) ተናግረዋል፡፡
አቶ ዘመዴነህ በበኩላቸው፣ ድርጅታቸው በኢትዮጵያ የተለያዩ የልማት ድርጅቶችን በማማከር፣ በዋጋ ትመና፣ በትንተናና ስትራቴጂ በመንደፍ ልምድ አለው፡፡
‹‹ያልንን ልምድ ተጠቅመን ጥናቱን ከስምንት እስከ 12 ወራት ባሉት ጊዜያት እናጠናቅቃለን፤›› ሲሉ አቶ ዘመዴነህ አስረድተዋል፡፡
በኢትዮጵያ አብዛኞቹ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ያላቸውን ሀብት በቅጡ የማያውቁ ከመሆኑም በላይ፣ ያላቸውን ሀብት በዋጋ አሥልተው መረጃ የያዙት ጥቂቶች ናቸው፡፡
አብዛኞቹ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች መጋዘኖች ለዓመታት የተከማቹ ንብረቶች ሲኖሯቸው፣ ብዙዎቹን ንብረቶች በአግባቡ ስለማያውቋቸው አዳዲስ ተደጋጋሚ ግዥዎች በመፈጸም የአገር ሀብት እንደሚያባክኑ ይነገራል፡፡