ኩባንያው ይፋ ባደረገው መረጃ መሠረት በዕቅድ ከተያዘው 17 ሚሊዮን ብር የትርፍ መጠን አንፃር ሲታይ ከዕቅድ በላይ ትርፍ አስመዝግቧል፡፡ ኩባንያው በ2009 ዓ.ም. 9.6 ሚሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ አስመዝግቦ ነበር፡፡ የ2010 ዓ.ም. ትርፉ ከካቻምናው ሲነፃፀር የ115 በመቶ ዕድገት እንደታየበት አስታውቋል፡፡
በ2010 ዓ.ም. የኩባንያው ዓመታዊ የተመዘገበ የገቢ መጠንም ወደ 104.3 ሚሊዮን ብር ከፍ በማለቱ ከካቻምናው አኳያ መጠነኛ ለውጥ በማሳየት የአምስት በመቶ ጭማሪ አስተናግዷል፡፡ ከጠቅላላው የዓረቦን መጠን ውስጥ የተሽከርካሪ ኢንሹራንስ የአንበሳውን ድርሻ በመያዝ 59 በመቶ፣ በገንዘብ ሲሰላም የ61.3 ሚሊዮን ብር ድርሻ ይዟል፡፡ የገንዘብ ነክ ኢንሹራንስ 16 በመቶ ወይም 16.4 ሚሊዮን ብር በማስመዝገብ በሁለተኛ ደረጃ ይከተላል፡፡
በሒሳብ ዓመቱ የቀረቡ የጉዳት ካሳ ጥያቄዎችን በተመለከተ ኩባንያው 66.6 ሚሊዮን ብር የነበረ ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥም 50.1 በመቶ የሚሆነው ክፍያ ተፈጽሟል፡፡ ከአጠቃላይ የካሳ ክፍያ ጥያቄዎች ውስጥ 43.5 ሚሊዮን ብር ወይም 65 በመቶ የሚሆነው የተመዘገበው በተሽከርካሪ ኢንሹራንስ እንደነበር ያመለክታል፡፡
ኩባንያው በሒሳብ ዓመቱ ጠቅላላ የካሳ ክፍያ የዋለው 66.6 ሚሊዮን ብር ከባለፈው የሒሳብ ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር በ16.1 ሚሊዮን ብር ወይም በ19 በመቶ ቀንሶ ይታያል፡፡ በቀዳሚው ዓመት ለካሳ ክፍያ የዋለው 82.7 ሚሊዮን ብር ነበር፡፡ ይህም የሚያሳየው፣ የቀረበው የካሳ ክፍያ የሎስ ሬሾ መጠን ወደ 58 በመቶ በመሆን ባለፈው ዓመት 76 በመቶ ከነበረው ጋር ሲነፃፀር በእጅጉ ቀንሶ መገኘቱን ነው፡፡
ኩባንያው በተጠናቀቀው የሒሳብ ዓመት ከውል ሽያጭ 34.3 ሚሊዮን ብር እንዳስመዘገበ የሚገልጸው የኩባንያው መረጃ፣ ካቻምና ከነበረው 18.4 ሚሊዮን ጋር ሲነፃፀር የ15.9 ሚሊዮን ብር ወይም የ86 በመቶ ብልጫ እንደተገኘበት ያሳያል፡፡ ኩባንያው ይኼንን ለውጥ ማስመዝገብ የቻለበት አንዱ ምክንያት፣ በኩባንያው ላይ ከፍተኛ ወጪ ሲያስከትሉ በነበሩ የተሽከርካሪ ዓይነቶች ላይ ከፍተኛ የዓረቦን ክፍያ መሻሻያ በማድረግ የኩባንያው ማኔጅመንት ዕርምጃ በመውሰዱ እንደሆነ በሪፖርቱ አስፍሯል፡፡
እንደ ኩባንያው መረጃ የኩባንያው ጠቅላላ ሀብት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት መጨረሻ ላይ 316.2 ሚሊዮን ብር ደርሷል፡፡ ይህም የገንዘብ መጠን 45.6 ሚሊዮን ብር ወይም 17 በመቶ ዕድገት ያሳየ ሲሆን፣ ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ከተመዘገበው ከ270.6 ሚሊዮን ብር ጋር ሲነፃፀር የተሻለ መሆኑን ያመለክታል ተብሏል፡፡