ሕሙማኑ መንገድ ላይ ሳይለምኑ እንዲታከሙ ገንዘብ የማሰባሰብ ሥራ ተጀምሯል
የኩላሊት ሕመምተኛ መሆናቸውን በመግለጽ በመኪና ላይ ወይም በጎዳና በመሆንና በድምፅ ማጉያ በመጠቀም፣ የገንዘብ ዕርዳታ የሚጠይቁ ሕሙማንን ከልመና አውጥቶ ለማሳከም ‹‹ከራስ ቆርሶ ለራስ መስጠት›› በሚል መሪ ቃል በጎ ፈቃደኞች ገንዘብ መለገስ የሚችሉበት አሠራር መዘርጋቱን የኩላሊት ሕመምተኞች እጥበት በጎ አድራጎት ድርጅት አስታወቀ፡፡
የድርጅቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ ሰሎሞን አሰፋ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ሕሙማኑ መንገድ ላይ ሳይለምኑ ሕክምና እንዲያገኙ ለማስቻል በኢትዮጵያ ካሉት 17 ባንኮች ዋና መሥሪያ ቤቶችና ከ4,193 ቅርንጫፍ መሥሪያ ቤቶች ጋር አብሮ መሥራት ተጀምሯል፡፡
በባንኮቹ የሚሠሩ በርካታ ሠራተኞች ሕሙማኑን ለመርዳት የገንዘብ ድጋፍ መጀመራቸውን በቀጣይም ሁሉም ሠራተኞች ድጋፍ ያደርጋሉ ተብሎ እንደሚታመን በመግለጽም፣ በባንኮቹ የተከፈቱ የሒሳብ ደብተሮችን ቁጥር ከየባንኩ ሰሌዳ ላይ በማንበብ መርዳት የሚፈልግ ሁሉ ገንዘብ ገቢ ማድረግ እንደሚችልም ተናግረዋል፡፡
በየመንገዱ በግለሰብ ደረጃ ከሚለመን፣ በጎፈቃደኞችን በማስተባበር ሁሉም የተቸገሩ የኩላሊት ሕሙማን ሕክምና የሚያገኙበትን ሥርዓት ለመዘርጋት አሠራሩን ተቋማዊ ማድረግ እንደሚገባም አክለዋል፡፡
ድርጅቱ አሠራሩን ተቋማዊ በማድረግ ሕሙማኑን ለመድረስ የጀመረውን እንቅስቃሴ ኅብረተሰቡ እንዲደግፈው ጥሪ ያቀረበ ሲሆን፣ ከባንኮቹ በተጨማሪ ለ40 ድርጅቶችም ደብዳቤ ማስገባታቸውን ተናግረዋል፡፡
በየመሥሪያ ቤቱ ያሉ ሠራተኞች ከደመወዛቸው የተቻላቸውን ያህል በባንኮቹ በተከፈቱ የሒሳብ ደብተሮች ገቢ በማድረግም የኩላሊት ሕሙማኑን ከመንገድ ላይ ልመና እንዲታገዱ ጠይቀዋል፡፡
ሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል የተቻለውን እንዲረዳ፣ በድርጅቱ በኩልም ገቢ የተደረገውን ገንዘብና ለሕክምና የዋለውን በተመለከተ በየጊዜው ይፋ እንደሚደረግ አቶ ሰሎሞን ገልጸዋል፡፡
በኢትዮጵያ የኩላሊት እጥበት የሚያስፈልጋቸው ሕሙማን ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱን የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ከዚህ ቀደም ማስታወቁ ይታወሳል፡፡