– አቶ ጌታቸው አሰፋን የተመለከተ አጀንዳ አልነበረም
የሕወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ሰሞኑን የተሰበሰበው መደበኛውን የሥራ አፈጻጸም ግምገማ ለማድረግ ሲሆን፣ በዚህም መሠረት የክልሉ መንግሥት ካለፈው ሐምሌ ወር 2010 ዓ.ም. ወዲህ ባሉት ጊዜያት ያከናወናቸውን ሥራዎች እንዲሁም ፀጥታና ደኅንነትን በተመለከቱ ጉዳዮች ላይ ግምገማ ማድረጉን የድርጅቱ ሥራ አስፈጻሚ አባል አቶ ጌታቸው ረዳ ለሪፖርተር ገለጹ።
ሕወሓት ለሁለት ቀናት ያካሄደውን ስብሰባ ባለፈው ዓርብ አጠናቋል። ይህ ስብሰባ የተለየ አለመሆኑን የተናገሩት አቶ ጌታቸው ረዳ፣ በፓርቲ ደረጃ በመገናኘት የክልሉን መንግሥት የሥራ አፈጻጸምና ወቅታዊ ሁኔታዎች ከተገመገሙ ቆየት በማለቱ የተጠራ ስብሰባ ቢሆንም የተለመደ የፓርቲ ሥነ ሥርዓት መሆኑንም አመልክተዋል።
በዚህ ስብሰባ የክልሉ መንግሥት ባለፉት ወራት ያከናወናቸው የልማትና የማኅበራዊ ጉዳዮች ሲገመገሙ፣ በተጨማሪም በወቅታዊ የፀጥታና ደኅንነት ጉዳዮች ላይ ውይይት መካሄዱን ተናግረዋል።
አቶ ጌታቸው ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የሕወሓት ዋነኛ መወያያ አጀንዳ ባይሆንም ከወራት በፊት የተከፈተው የኢትዮ ኤርትራ ድንበር በቅርቡ የተዘጋበት ምክንያት ምን እንደሆነ የክልሉ ምክትል ፕሬዝዳንትና የሕወሓት ሊቀመንበር ደብረጽዮን ገብረ ሚካኤል (ዶ/ር) ማብራሪያ እንዲሰጡበት ጥያቄ ቀርቦላቸው ነበር።
ጉዳዩ በቀጥታ የፌዴራል መንግሥትን የሚመለከት ቢሆንም፣ ጉዳዩን የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት እንዲከታተሉት ማዕከላዊ ኮሚቴው መስማማቱን ገልጸዋል።
በክልሉ የፀጥታና ደኅንነት ጉዳዮች እንዲሁም በአገር ደረጃ የሚስተዋለው የፀጥታ ችግርን በተመለከተ ውይይት መደረጉን የገለጹት አቶ ጌታቸው ረዳ፣ ምንም እንኳን ሕወሓት በአገር አቀፍ ደረጃ ያለው ሚና ትንሽ ቢሆንም ከፌዴራል መንግሥት ጋር በመተባበር ኃላፊነቱን እንዲወጣ መወሰኑን ተናግረዋል።
የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ በዚህ ሳምንት ለፓርላማ ባቀረበው ሪፖርት በከባድ የሰብዓዊ መብት ወንጀል የተጠረጠሩት የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት የቀድሞ ዋና ዳይሬክተር አቶ ጌታቸው አሰፋ በቁጥጥር ሥር ለማዋል ለትግራይ ክልል ጥያቄ ቢቀርብም ክልሉ ለመተባበር ፈቃደኛ አለመሆኑና የክልሉ አመራር አቶ ጌታቸውንም ሆነ ሌሎች ተጠርጣሪዎችን ሸሽጓል በማለት ዋና ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ አቶ ብርሃኑ ጸጋዬ ተናግረው ነበር።
የሕወሓት ስብሰባ ከዚህ ወቀሳ በኋላ የተካሄደ በመሆኑ የአቶ ጌታቸው ጉዳይ የውይይቱ አካል ይሆናል የሚል ግምት በበርካቶች ዘንድ ነበር።
የአቶ ጌታቸው አሰፋን ጉዳይ የተመለከተ ውይይት ተካሄዶ እንደሆነ የተጠየቁት አቶ ጌታቸው ረዳ፣ በዚህ ጉዳይ ላይ ውይይት አለመደረጉንና ፓርቲው በጉዳዩ ላይ ሊወያይም እንደማይችል ተናግረዋል።
አቶ ጌታቸው አሰፋ የሕወሓት ሥራ አስፈጻሚ አባል መሆናቸው ይታወቃል፡፡ ነገር ግን በዚህ የሕወሓት ስብሰባ ላይ አለመገኘታቸውን ሪፖርተር ከአቶ ጌታቸው ረዳ ለማረጋገጥ ችሏል።
በኢሕአዴግ መተዳደሪያ ደንብ መሠረት የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ በየሦስት ወሩ፣ ማዕከላዊ ኮሚቴው ደግሞ በየስድስት ወሩ መገናኘት እንዳለበት ቢደነግግም፣ አስቸኳይ ሁኔታዎች ሲኖሩ ሊጠራ እንደሚችል ይደነግጋል።
ይሁን እንጂ ሥራ አስፈጻሚው ከተሰበሰበ ቆይቷል። ይህ ጉዳይ በሕወሓት የሰሞኑ ስብሰባ ተነስቶ እንደሆነ የተጠየቁት አቶ ጌታቸው፣ ‹‹አልተነሳም። ሕወሓት በዚህ ጉዳይ ለምን ይወያያል? ስብሰባውን መጥራት ያለበት የኢሕአዴግ ሊቀመንበር ነው፤›› ብለዋል።
ነገር ግን የአገሪቱ ወቅታዊ የፀጥታና የደኅንነት ጉዳዮች በኢሕአዴግ ደረጃ ውይይት ሊደረግባቸው እንደሚገባ የተናገሩት አቶ ጌታቸው ረዳ፣ ‹‹ኢሕአዴግ በቅርቡ ስብሰባ ካልጠራ በእኛ በኩል ስብሰባ እንዲጠራ ጥያቄ ልናቀርብ እንችላለን፤›› ብለዋል።
በማኅበራዊ ትስስር ገጾች የሕወሓት ሊቀመንበር ከኃላፊነት ለመልቀቅ ጥያቄ አቅርበው እንደነበር የሚወራውንም አስተባብለዋል።