ከሁለት አሠርታት በላይ ያስቆጠረው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ካለፈው ሁለትና ሦስት ዓመታት ወዲህ ከውጤት በተጓዳኝ የገጠመው ትልቅ ፈተና ቢኖር የስፖርታዊ ጨዋነት መዛነፍ ይጠቀሳል፡፡ ችግሩ በጊዜ ሒደት ከመሻሻል ይልቅ ብሔርና ቋንቋን መሠረት በማድረግ የአንድ ክልል ክለብ ወደ ሌላ ክልል ተንቀሳቅሶ ጨዋታን ለማድረግ ተቸግሮ የነበረ ለመሆኑ የአማራና የትግራይ ክልል ክለቦችን ለአብነት መጥቀሱ በቂ ይሆናል፡፡
የሁለቱ ክልሎች ክለቦች ባለፈው የውድድር ዓመት አጋማሽ ጀምሮ በየሜዳዎቻቸው ማድረግ የነበረባቸውን ጨዋታ በገለልተኛ ሜዳ ማለትም በአዲስ አበባ ስታዲየም እንዲያከናውኑ ተወስኖ ፕሮግራሙን ማጠናቀቃቸው አይዘነጋም፡፡ በወቅቱ የነበረው የፌዴሬሽን አመራር ችግሩን በእንጭጩ መቋጨት ሲገባው ምንም ባለማድረጉ ልዩነቱ እየሰፋ እንዲመጣ መነሻ ሆኖ ወደ 2011 የውድድር ዓመት እንዲሸጋገር ምክንያት ስለመሆኑ ጭምር የሚናገሩ አሉ፡፡
በውድድር ዓመቱ አጋማሽ ላይ የፌዴሬሽኑን ኃላፊነት በምርጫ የተረከበው የአቶ ኢሳያስ ጅራ ካቢኔ በበኩሉ፣ የ2011 የውድድር ዓመት ከመጀመሩ አስቀድሞ ችግሩን ቀርፎ የፕሪሚየር ሊጉ መደበኛ የተዟዙሮ ጨዋታ እንዲቀጥል ለማድረግ ጥረት ቢያደርግም ባለመሳካቱ ጥቅምት 17 ቀን 2011 ዓ.ም. የተጀመረው የሊጉ መርሐ ግብር እንዲቆራረጥ አድርጎ ቆይቷል፡፡ በሁለቱ ክልሎች የተጀመረው አንዱ በሌላው ሜዳ ‹‹ሄጄ አልጫወትም›› የሚለው የአፈንጋጭነት ባህርይ ለስፖርቱ ተጨማሪ ራስ ምታት እንዲሆን ማድረጉ አልቀረም ነበር፡፡
ጅምሩ ያልተመቸው የብሔራዊ ፌዴሬሽኑ አመራሮች በተለይ ከአማራና ከትግራይ ከፍተኛ አመራሮች ጋር በአካል በመገናኘት ችግሩ መፍትሔ ያገኝ ዘንድ ጥረት አድርገዋል፡፡ የየክልሎቹ ሊቃነ መናብርት ክለቦቻቸው አንዱ ወደ ሌላው ሄደው መጫወት እንደሚችሉ ቃል ቢገቡም እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ፌዴሬሽኑ ያወጣውን መርሐ ግብር ለመተግበር ቅድሚያውን ወስዶ ይሁንታ የሰጠ አልነበረም፡፡
ይሁንና ባለፈው ሳምንት ወደ ትግራይ ያመሩት ሁለቱ የአማራ ክለቦች ፋሲል ከተማና በከፍተኛ ሊግ እየተወዳደረ የሚገኘው ደሴ ከተማ ችግሩ እልባት እንዲያገኝ ትልቁን ድርሻ መወጣታቸው ተዘግቧል፡፡ የአስተናጋጆቹ መቐለና የአክሱም ከተማ ነዋሪዎችና ስፖርት ወዳዱ ኅብረተሰብ እንግዶቻቸውን የተቀበሉበት አግባብ ‹‹ፖለቲካውን ለፖለቲከኞች›› የሚል አንድምታ ያለውን መልዕክት በግልጽ አስተላልፏል፡፡ የታየው ወንድማዊ አቀባበልና መስተንግዶ ለሰላማዊ እንቅስቃሴ ብቻ ሳይሆን ለእግር ኳሱ ዕድገት ጭምር የጎላ ድርሻ እንዳለው ሌሎችም ሊማሩበት እንደሚገባ አመላካች መሆኑ አያጠያይቅም፡፡ ከእግር ኳስ ሦስት መገለጫዎች ማሸነፍ፣ መሸነፍና አቻ መውጣት መሆኑን ያልተረዱ አንዳንዶች በተለይ በፕሪሚየር ሊጉ የሚጫወቱት አስተናጋጁ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲና እንግዳው ፋሲል ከተማ በጨዋታው ነጥብ ተጋርተው መውጣቸው ጥያቄ የሆነባቸው አልጠፉም፡፡