የጅማ አባ ጅፋር እግር ኳስ ክለብ ፕሪሚየር ሊጉን በተቀላቀለበት ዓመት የሊጉን ዋንጫ በማንሳት ለውድድር ዓመቱ ኢትዮጵያን በመወከል በአፍሪካ የክለቦች ሻምፒዮና ላይ በመሳተፍ በአንደኛ ዙር በግብፁ አል አህሊ ከተሰናበተ በኋላ ወደ ኮንፌዴሬሽኑ ዋንጫ ተሸጋግሮ በሞሮኮው አሳኒያ አጋዲ በግማሽ ደርዘን አካባቢ የጎል ልዩነት ተሸንፎ ከመድረኩ መሰናበቱ ይታወሳል፡፡ በኮንፌዴሬሽኑ ዋንጫ ሌላው የአገሪቱ ተወካይ የነበረው መከላከያም በናይጀሪያው ኢኑጉ ሬንጀርስ በደርሶ መልሱ ጨዋታ ተመሳሳይ የጎል ዕዳ ይዞ በጊዜ መሰናበቱ አይዘነጋም፡፡
የሁለቱ ክለቦች ውክልናና በመድረኩ ሊኖራቸው ይገባል ተብሎ በሚታሰበው የተፎካካሪነት አቅምን የተመለከቱ አስተያየቶችና ትችቶች እንዲሁም አንድ ክለብ ከውጤቱ ጎን ለጎን ሊይዝ ስለሚገባው የአደረጃጀት ቅርፅና ይዘት ጭምር ብዙ ሲባል ቆይቷል፣ እየተባለም ይገኛል፡፡ በተለይ ከአፍሪካ የክለቦች ሻምፒዮናው በጊዜ ተሰናብቶ ወደ ኮንፌዴሬሽኑ ዋንጫ የተሸጋገረው ጅማ አባ ጅፋር በመድረኩ ካስመዘገበው ውጤት ባሻገር ክለቡ የሚመራበት አስተዳደራዊ ሥርዓትና የጉዞ ሁኔታ አግራሞትን መፍጠሩ ብዙዎችን ማነጋገሩ አልቀረም፡፡
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ2010 የውድድር ዓመት አሸናፊው ጅማ አባ ጅፋር በአፍሪካ የክለቦች ሻምፒዮና የቅድመ ማጣሪያ ተጋጣሚው የጅቡቲው ቴሌኮምን ጥሎ፣ በአንደኛው ዙር በግብፁ አልአህሊ ነበር ከመድረኩ የተሰናበተው፡፡ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) የአኅጉሪቱን ክለቦች የተፎካካሪነት አቅም ለማጎልበት በሚከተለው የአሠራር ሥርዓት አንድ ቡድን ጥሎ በሁለተኛው ዙር የሚሸነፍ ክለብ ለአፍሪካ የክለቦች ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ተሳትፎ ይበቃል በሚለው አሠራር መሠረት ነበር ጅማ አባ ጅፋር የዕድሉ ተጠቃሚ የሆነው፡፡
ይሁንና በሞሮኮው አሳኒያ አጋዲ በሜዳው በተቆጠረበት አንድ ጎልና ከሜዳው ውጪ ባስተናገደው አራት ጎል በድምሩ 5 ለ0 በሆነ ሰፊ ውጤት ተሸንፎ ከሻምፒዮናው መውጣቱ በውጤት ደረጃ ሲለካ፣ የክለቡ አስተዳደር ለጨዋታ ዝግጅትና ጉዞ ሲከተለው የነበረው የአሠራር ሥርዓት ሰሞንኛ መነጋገሪያ እንደሆነ ይገኛል፡፡
ክለቡ መጀመርያ ወደ ግብፅ በነበረው ጉዞ ‹‹ሠርገኛ መጣ›› ዓይነት በ11ኛው ሰዓት ከብዙ ውጣ ውረድ በኋላ መሳካቱ አይዘነጋም፡፡ በዚህ ያልተማረው ጅማ አባ ጅፋር የሞሮኮ ዝግጅትና ጉዞ እጅጉን ለትዝብት ያጋለጠው እንደነበር ታይቷል፡፡ 15 ተጨዋቾችና አንድ አሠልጣኝ በሁለት ዙር ወደ ሞሮኮ ሲያቀኑ ከቡድኑ ጋር መጓዝ የነበረባቸው ምክትል አሠልጣኞችና ቀሪ ተጨዋቾች አንዲቀሩ መደረጉ አግባብ እንዳልሆነ ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ የቡድኑ አባላት ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
እንደ አስተያየት ሰጪዎቹ ከሆነ፣ ‹‹ክለቡ ለአኅጉራዊው መድረክ መብቃቱ የተረጋገጠው ቀደም ብሎ መሆኑ ይታወቃል፡፡ በመሆኑም ክለቡን የሚያስተዳድረው አካል እንደነዚህ የመሰሉ በተለይም ከወጪ ጋር የተያያዙ ችግሮች እንዳያጋጥሙ ቀደም ብሎ ማሰብ ነበረበት፤›› በማለት ያለውን የተዝረከረከ አሠራርና ሥርዓት ይተቻሉ፡፡