በቅርቡ ኢትዮጵያን በተለያዩ አገሮች እንዲወክሉ የተሾሙ 20 አምባሳደሮችና ሁለት ምክትል የሚሲዮን መሪዎች የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅምና በተመደቡበት አገሮች ያሉ ኢትዮጵያውን ዜጎችን ጉዳይ ቅድሚያ ሰጥተው ሊሠሩ እንደሚገባ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) አስገነዘቡ፡፡
ሚኒስትሩ ይህን ማሳሰቢያ የሰጡት ለአሥር ቀናት የሚቆየውንና ሰኞ ጥር 20 ቀን 2011 ዓ.ም. የተጀመረውን፣ ለተሿሚ አምባሳደሮች የሚሰጠውን ሥልጠና በይፋ በከፈቱበት ወቅት ነው፡፡
ሥልጠናው በዲፕሎማሲና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዙሪያ ከሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ፣ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲና ከተለያዩ ተቋማት በተውጣጡ የዘርፉ ባለሙያዎች የሚሰጥ ነው፡፡
ከእስካሁኑ የአምባሳደሮች ሥልጠና በተለየ በዚህኛው ሥልጠና የአምባሳደሮቹ የትዳር አጋሮች የሥልጠናው ተካፋይ እንደሚሆኑም፣ ሚኒስትሩ በሥልጠናው መክፈቻ ወቅት ተናግረዋል፡፡
ዲፕሎማቶቹ ከተለያዩ የሥራ መስኮችና ልምድ መምጣታቸው መልካም አጋጣሚ እንደሆነ የገለጹት ሚኒስትሩ፣ ያካበቱትን የሥራና የዕውቀት ልምድ ዲፕሎማሲው ከሚመራበት ንድፈ ሐሳብና አሠራሮች ጋር በማዋሀድ የአገሪቱን ብሔራዊ ጥቅም፣ እንዲሁም የዜጎችን መብትና ጥቅሞች ማስጠበቅ እንደሚገባቸው አሳስበዋል፡፡
‹የ21ኛው ክፍለ ዘመን ዲፕሎማሲ በበርካታ ዕድሎችና ተግዳሮቶች የተሞላ ነው፡፡ ይህንን ዕድልም ሆነ ተስፋ ዜጎችን በማሳተፍ የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ ይቻላል፡፡ ባለንበት ዘመን የአገሮች ጥንካሬ የሚለካውም ባስመዘገቡት የዲፕሎማሲ ስኬት ስለሆነ፣ ክህሎታችሁን በየጊዜው በማዳበር አገራችን በዲፕሎማሲ መስክ ያላትን የካበተ ስምና ዝና አጠናክሮ ማስቀጠል ይጠበቅባችኋል፤›› በማለት ከተሿሚዎቹ አምባሳደሮች የሚጠበቀውን የሥራ ኃላፊነት አብራርተዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) በቅርቡ ኢትዮጵያን በተለያዩ አገሮች ለሚወክሉ አምባሳደሮችና የውጭ ጉዳይ አመራሮች በውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ማሻሻያ፣ እንዲሁም ዲፕሎማቶች በቀጣይ ሊያተኩሩባቸው ስለሚገቡ ጉዳዮች አቅጣጫና መመርያ መስጠታቸው የሚታወስ ነው፡፡