የጅማ አባ ጅፋር እግር ኳስ ክለብ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ከሚያከናውናቸው ውድድሮች መታገዱን ተቃወመ፡፡
ክለቡ የዲሲፒሊን ውሳኔን ተግባራዊ ባለማድረጉ የተነሳ ከየካቲት 29 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ ፌዴሬሽኑ ከሚያዘጋጃቸው ማንኛውም ውድድሮች መታገዱን ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ አስታውቆ ነበር፡፡
ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ በላከው መረጃ መሠረት አብዱልፈታ ካሚል የተባለ የክለቡ ተጫዋች ከክለቡ ጋር ውል እያለው ከመስከረም ወር 2010 ዓ.ም. ጀምሮ ውሉ በክለቡ በመቋረጡ ባቀረበው አቤቱታ የዲሲፕሊን ኮሚቴ ተመልክቶ ያልተከፈለውን ደመወዝ ታስቦ በአምስት ቀናት ውስጥ እንዲከፈለው ቢያዝም አለመከፈሉ የዕገዳው መንስዔ መሆኑን መረጃው ያትታል፡፡
የብሔራዊ ፌዴሬሽኑ የዕግድ ውሳኔ በክለቡ ተቃውሞ ገጥሞታል፡፡ ክለቡ ውሳኔውን ተከትሎ ግብረ መልስ መስጠቱን ገልጾ ተጫዋቹ አልተከፈለኝም ያለውን ቀሪ የስድስት ወር ክፍያ በየወሩ 30 ሺሕ ብር (ከታክስ በፊት) ለመክፈል ፈቃደኛ መሆኑን የክለቡ ፕሬዚዳንት አቶ ሃጃይባ አባመጫ ለሪፖርተር አስረድተዋል፡፡ ‹‹ተጫዋቹ ያልሠራበትን ክፍያ መጠየቁን ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ እያወቀ፣ እንደዚህ ዓይነት ውሳኔ መወሰኑ አግባብ አይደለም፤›› በማለት አቶ ሃጃይባ ቅሬታቸውን ሳይገልጹ አላለፉም፡፡
ክለቡ በ2009 ዓ.ም. ስድስት ተጫዋቾችን ከተለያዩ ክለቦች ያስፈረመ ቢሆንም ብቃታቸው አይመጥንም ያላቸውን ማባረሩንና ቅሬታ አቅራቢው አንዱ መሆኑና ተጫዋች ያልሠራበትን መጠየቁ ተገቢ አይደለም ይላሉ፡፡
በሌላ በኩል በክለቡ ላይ በተደጋጋሚ ሲነሳ የሰነበተው የተጫዋቾች ደመወዝ ክፍያ ችግር አንድ ወይም ሁለት ወራት ከመዘግየቱ በቀር ምንም ዓይነት ችግር እንደሌለ ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል፡፡