Sunday, March 26, 2023
- ማስታወቂያ -
- ማስታወቂያ -

ጃፓን ቀዳሚ ከሆነችበት የዓለም ዕዳ ተሸካሚ አገሮች ተርታ ኢትዮጵያ በ40ዎቹ ትከተላለች

- ማስታወቂያ -

ተዛማጅ ፅሁፎች

የኢትዮጵያ የዕዳ ጫና በየጊዜው እየጨመረ በመምጣት በአሁኑ ወቅት መበደር ወደማትችልበት ደረጃ አድርሷታል፡፡ መንግሥት ቢያንስ የአጭር ጊዜና ከፍተኛ ወለድ የሚታሰብባቸውን ብድሮች ለማቆም ተገዷል፡፡ በአንፃሩ ከብድር ይልቅ ዕዳ ክፍያ ላይ እንዲያተኩር አስገዳጅ ሁኔታ ውስጥ ወድቋል፡፡ ይሁንና በዓለም ከፍተኛ ዕዳ ከተሸከሙ አገሮች ውስጥ ጃፓን በቀዳሚነት ስትቀመጥ፣ ኢትዮጵያ ከ130 አገሮች ውስጥ ከ49ኛዋ በመሆን ከዋና ዋና ባለዕዳዎች ተርታ ተመድባለች፡፡

ፎከስ ኢኮኖሚክስ የተሰኘው ድረ ገጽ ባወጣው የአገሮች ዝርዝር መሠረት፣ የኢትዮጵያ ዕዳ ከጠቅላላ ኢኪኖሚዋ (ከጠቅላላ የአገር ውስጥ ምርት አኳያ) 58 በመቶ ስለመድረሱ የሚያጣቅስ አኃዝ አቅርቧል፡፡ ይሁንና ቅርብ ጊዜ መረጃዎች ግን አኃዙ ከ60 በመቶ በላይ መሻገሩን ይጠቁማሉ፡፡ ይህም ሆኖ ይህን ያህሉ የዕዳ መጠን ለመጪዎቹ ዓመታትም ባለበት እንደሚቆይ ድረ ገጹ በሪፖርቱ ባመላከተው ትንበያ አስፍሯል፡፡ እ.ኤ.አ. በ2023 የኢትዮጵያ የዕዳ መጠን ከኢኮኖሚዋ 55 በመቶ እንደሚሸፍን ተገምቷል፡፡ ይህ እንግዲህ በዓመት ከአንድ ቢሊዮን ዶላር በላይ ለዕዳ ክፍያ እንደሚውል የሚጠበቅ የዕዳ መጠን ነው፡፡ በዚህ ዓመት ብቻ መንግሥት ከ22 ቢሊዮን ብር ያላነሰ ገንዘብ ለዕዳ ክፍያ እንደሚያውል ቀደም ብሎ ማስታወቁ ይታወሳል፡፡ ባለፈው ዓመት ከ16 ቢሊዮን ብር በላይ ለዕዳ ክፍያ ውሏል፡፡

እንደ ኢትዮጵያ ያሉ ደሃ አገሮች እ.ኤ.አ. በ2005 በተካሄደው የቡድን ሰባት አገሮች ስብሰባ ወቅት፣ ግሌንኢግልስ እየተባለ በሚጠራው ስምምነት መሠረት አብዛኛው ዕዳቸው እንዲሰረዝላቸው ተወስኖ ነበር፡፡ ይሁንና ከዚህ የዕዳ ስረዛ በኋላም አብዛኞቹ ድሆች አገሮች በአማካይ የኢኮኖሚያቸውን 40 በመቶ ድረስ የሚሸፍን የዕዳ ጫና ውስጥ ገብተዋል፡፡

የኢኮኖሚዋን 230 በመቶ በዕዳ ጫና ውስጥ የምትገኘው ጃፓን፣ ምናልባትም በፋይናንስ ቀውስ ልትመታ የምትችልበት ሰፊ አደጋ እንደተጋረጠባት ምሁራኖቿ ያስጠነቅቃሉ፡፡ ምንም እንኳ ከጃፓን አኳያ ሲታይ፣ የኢትዮጵያ ዕዳ እዚህ ግባ የሚባል ባይመስልም ከኢትዮጵያ የኢኮኖሚ አቅም አኳያ ግን ኢትዮጵያ ከፍተኛ የዕዳ ጫና ውስጥ እንደምትገኝ የቅርብ ጊዜ የዓለም የገንዘብ ድርጅት መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ መካከለኛ ከሚባለው የዕዳ ጫና ወደ አሳሳቢ የዕዳ ጫና ክልል ገብታለች፡፡

በአሁኑ ወቅት ከውጭም ከአገር ውስጥ ምንጮችም ተዳምሮ የኢትዮጵያ መንግሥት ዕዳ ከ50 ቢሊዮን ዶላር በላይ ይገመታል፡፡ በአንፃሩ የጃፓን ዕዳ 12 ትሪሊዮን ዶላር ገደማ ነው፡፡ በጃፓን ፊት አውራሪነት የሚመሩት የዓለም አሥር ዋና ዋና ባለዕዳዎች ግሪክ፣ ሊባኖስ፣ በፖለቲካ የምትታመሰው ቬንዙዌላ፣ ጣልያን፣ ሞዛምቢክ፣ አሜሪካና ቤልጂየም ናቸው፡፡

ከእነዚህ አገሮች በተለይ እንደ ግሪክ ያሉቱ አስከፊ የኢኮኖሚ ቀውስ ለማስተናገድ የተዳረጉ ናቸው፡፡ ምንም እንኳ ጃፓን በበዓለም ካሉ ከፍተኛ ዕዳ ተሸካሚ አገሮች ዋናዋ ብትሆንም እንደ እነግሪክ አልተንኮታኮተችም፡፡ ይኸውም ኢኮኖሚዋ የዕዳ ጫና የመሸከም አቅሙ ከፍተኛ ከመሆኑም በላይ እንደ እነግሪክ በፍጆታና ከውጭ በሚገባ ሸቀጥ አለመጥለቅለቋ አንዱ ምክንያት ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ደጋግመው በምሳሌ የሚያነሷት ግሪክ፣ ውብ ደሴቶቿን ለግል ባለሀብቶች ለመሸጥ የተገደደች፣ ሕዝቧ ባንክ ያስቀመጠውን ገንዘብ እንዳያወጣ ገደብ ያስቀመጠችና በ21ኛው ክፍለ ዘመን የተንኮታኮተች የአውሮፓ ቁንጮ ነች፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በየስብሰባው ስለግሪክ በተናገሩ ቁጥር ከአንደበታቸው የሚደመጠው ግሪካውያን አገራቸው በፋይናንስና በኢኮኖሚ ቀውሶች ሳቢያ ከገባችበት ቀውስ ለመውጣት የገቢያቸውን እስከ 50 በመቶ በመደጎም፣ ያላቸውን ጌጣጌጥ፣ ‹‹የጣት ቀለበታቸውን›› ሳይቀር ለአገራቸው በመስጠት አገራቸውን ከአጣብቂኝ እንድትወጣ ለመታደግ ዜጎቿ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን ደጋግመው ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡  

spot_img
- Advertisement -spot_img

የ ጋዜጠኛው ሌሎች ፅሁፎች

- ማስታወቂያ -

በብዛት ከተነበቡ ፅሁፎች